23/02/2020
ሪህ—መንስኤውና ለበሽታው የሚያጋልጡ ነገሮች
ሪህ በጣም ከተለመዱት የአርትራይተስ በሽታ ዓይነቶች አንዱ ሲሆን ከፍተኛ ሥቃይ ሊያስከትል ይችላል። “ሪህ፣ ሰውነት ዩሪክ አሲድን በተገቢው መንገድ ማስወገድ ባለመቻሉ ምክንያት የሚመጣ ችግር” እንደሆነ አርትራይተስ የተባለው መጽሐፍ ገልጿል። መጽሐፉ አክሎም እንዲህ ብሏል፦ “ሪህ መንስኤው በግልጽ የሚታወቅ ሕመም ነው፤ ይህ ሕመም የሚከሰተው በመገጣጠሚያዎች መሃል ባለው ፈሳሽ (ሲኖቪያል ፍሉይድ) ውስጥ የዩሪክ አሲድ ቅንጣቶች ሲኖሩ ነው። ሪህ የሚያጠቃው መገጣጠሚያዎችን በተለይም በእግር አውራ ጣት ውስጥ የሚገኙትን ነው።”
ዩሪክ አሲድ፣ የሪህ በሽተኛ በሆኑ ሰዎች ደም ውስጥ የሚገኝ ከሰውነት ሊወገድ የሚገባ ነገር ነው፤ ዩሪክ አሲድ የሚፈጠረው ፕዩሪን ከተባሉት ንጥረ ነገሮች ነው። አብዛኛውን ጊዜ ዩሪክ አሲድ በሰውነት ውስጥ የሚጠራቀመው በሽንት አማካኝነት በተገቢው መጠን ባለመወገዱ ነው። በዚህ ጊዜ መርፌ መሰል የዩሪክ አሲድ ቅንጣቶች በእግር አውራ ጣት መገጣጠሚያ ላይ ሊከማቹ ይችላሉ፤ እርግጥ ነው፣ እነዚህ ቅንጣቶች በሌሎች የሰውነት መገጣጠሚያዎች ላይም ሊጠራቀሙ ይችላሉ። በዚህ ምክንያት መገጣጠሚያው ስለሚቆጣ ያብጣል ብሎም ከፍተኛ ሥቃይ ያስከትላል፤ እንዲሁም ሲነኩት ያተኩሳል።* አልፍሬድ የሚባል አንድ የሪህ ሕመምተኛ የታመመው ክፍል “በትንሹ ቢነካ እንኳ በጦር የተወጋ ያህል በጣም ያሠቃያል” ብሏል።
አርትራይተስ አውስትራሊያ ያወጣው መረጃ እንዲህ ይላል፦ “የሪህ ሕመም አንድ ጊዜ ከተቀሰቀሰ በኋላ ሕክምና ካላገኘ በአብዛኛው ለአንድ ሳምንት ያህል ይቆያል። ከዚያ በኋላ ለወራት እንዲያውም ለዓመታት ሕመሙ ድጋሚ ላይነሳ ይችላል። የሪህ ሕመምተኛ ተገቢውን ጥንቃቄ ካላደረገ ሕመሙ ቶሎ ቶሎ ሊቀሰቀስ፣ እያየለ ሊሄድ እንዲሁም በመገጣጠሚያዎች ላይ ዘላቂ የሆነ ጉዳት ሊያደርስ ይችላል። ሪህ ሥር የሰደደ ሕመም የሚሆንበት ጊዜም አለ።”
ሪህ በሕክምና ልንቆጣጠራቸው ከምንችል የአርትራይተስ ዓይነቶች አንዱ ነው። በሽታውን ለማከም በአብዛኛው የሚወሰዱት መድኃኒቶች ስቴሮይድ ያልሆኑ የሕመም ማስታገሻዎች ናቸው፤ በሽታው በተደጋጋሚ የሚያገረሽና ከፍተኛ ሥቃይ የሚያስከትል በሚሆንበት ጊዜ ደግሞ አሎፑሪኖል የተባለው ዩሪክ አሲድ እንዳይፈጠር የሚረዳ መድኃኒት ይወሰዳል። ሪህ እንዳያገረሽ ማድረግ ይቻላል? አዎ፣ ሕመምተኛው በሽታውን የሚያባብሱትን ነገሮች ካወቀ እንዳያገረሽበት ማድረግ ይችላል።
ሪህ እንዲያገረሽ የሚያደርጉ ነገሮች
ለሪህ በሽታ ዋነኛ መንስኤ የሚሆኑት ዕድሜ፣ ፆታና የዘር ውርስ ናቸው። አንዳንድ ሊቃውንት እንደሚሉት ከሆነ ከ50 በመቶ በላይ የሚሆኑት ሕመምተኞች በበሽታው የሚሠቃይ የቤተሰብ አባል ያላቸው ናቸው። ቀደም ሲል የተጠቀሰው አልፍሬድ “አባቴም ሆነ አያቴ ሪህ ነበራቸው” ብሏል። ከዚህም በላይ፣ ሪህ አብዛኛውን ጊዜ የሚያጠቃው ወንዶችን በተለይ ደግሞ በ40 እና በ50 ዓመት መካከል ያሉትን ነው። ወንዶች በበሽታው የመያዝ ዕድላቸው ከሴቶች በሦስት ወይም በአራት እጥፍ ይበልጣል፤ እንዲያውም ሴቶች ከማረጣቸው በፊት በበሽታው የመያዝ አጋጣሚያቸው እጅግ አነስተኛ ነው።
ከመጠን ያለፈ ውፍረትና አመጋገብ፦ ኢንሳይክሎፒድያ ኦቭ ሂውማን ኒውትሪሽን እንዲህ ይላል፦ “በአመጋገብ ሪህን ለመቆጣጠር የሚደረገው ጥረት በአሁኑ ጊዜ እያተኮረ ያለው ከፍተኛ የፕዩሪን ይዘት ያላቸው ምግቦችን በማስወገድ ላይ ሳይሆን ብዙ ጊዜ ከሪህ ጋር ተያያዥነት ያላቸው የጤና ችግሮችን ለምሳሌ ከመጠን ያለፈ ውፍረትን፣ ሰውነት ኢንሱሊንን በአግባቡ ጥቅም ላይ ባለማዋሉ ምክንያት የሚመጣ ሕመምን እንዲሁም ዲስሊፒዲሚያን በ