09/10/2025
ሪያል አጋፔ የጋብቻና ቤተሰብ የማማከር አገልግሎት ዓላማ የወንጌላውያን አብያተክርስቲያናት ጥንዶችን እና ቤተሰብ በጤናማ ክርስቲያናዊ ሥነምግባር እንዲታነፁና ጤናማ ማህበረሰብ እንዲኖር በእውነተኛ ፍቅር ላይ የተመሰረተ ትዳርና ጤናማ ቤተሰባዊ ግንኙነት እንዲሁም ማህበረሰብ በመፍጠር በሀገር ውስጥና ከሀገር ውጪ ሁለንተናዊ የምክርና የስልጠና አገልግሎት በመስጠት የክርስቶስ አካል እንዲሆኑ ማድረግ፡፡
ጋብቻ፣ ቤተሰብ እና ቤተክርስቲያን የተሳሰሩ እና ለጤናማና ለዳበረ ማኅበረሰብ መሠረት የሆኑ ምሰሶዎች ናቸው። በነዚህ ተቋማት ግንኙነት ላይ ያለው መጽሐፍ ቅዱሳዊ አመለካከት የእነዚህን ወሳኝ ተቋማት አስፈላጊነት እና እርስ በርስ መደጋገፍን የሚያስረዳ መለኮታዊ ማዕቀፍ ያመለክታል።
የዚህ ግንኙነት አስኳል የጋብቻ ተቋም ነው፣ እሱም በእግዚአብሔር የተደነገገ፣ በአንድ ወንድና በአንዲት ሴት መካከል ብቸኛ የሆነ የዕድሜ ልክ የቃል ኪዳን ጥምረት ነው (ዘፍጥረት 2፡24)፣ ቤተሰብ ደግሞ ከጋብቻ ቃል ኪዳን የተወለደ ነው፣ ቤተሰብ የህብረተ-ሰብ መሠረታዊ ክፍል ሆኖ ያገለግላል፣ የቤተሰብ መጽሐፍ ቅዱሳዊ ሞዴል የመብዛትን (የመራባትን) አስፈላጊነት፣ ልጆችን ማሳደግ እና የተረጋጋ የፍቅር አካባቢ መመስረትን ያጎላል (ዘፍጥረት 1፡28) ። መጪው ትውልድ በአለም አተያዩ እና ባህሪው በእሴቶቹ፣ በእምነቱ እና በባህሎቹ ተቀርጾና ተሞልቶ የሚያድገው በቤተሰብ ውስጥ ነው።
ቤተክርስቲያን እንደ መንፈሳዊ ተቋም የጤናማ ጋብቻ፣ የቤተሰብና የማህበረሰብ መገኛ ስለሆነች ጋብቻ ከቤተክርስቲያን ጋር ያለው መተሳሰር በመጽሐፍ ቅዱሳዊ ትረካ ውስጥ በግልጽ ይታያል፡፡ እነዚህ ተቋማት በእግዚአብሔር ለሰው ልጆች የመቤዠት እቅድ ውስጥ የጎላ ሚና አላቸው። በአዲስ ኪዳን ደቀመዛሙርት ወደ ዓለም ሲበተኑ ለክርስቶስ ቤተክርስቲያን መተከል ቤተሰብ ቀዳሚውን ድርሻ ይወስዳል፡፡
ሪያል አጋፔ የጋብቻና ቤተሰብ ማማከር አገልግሎት እንዚህን ተቋማት ለመገንባት ከወንጌላውያን አብያተ ክርስቲያናት ጋር በመቀናጀት ለመስራት እንዲሁም በጋብቻ ምክርና ትምህርት ቅዱሳንን ለማገልገል አገልግሎቱን የጀመረ መሆኑን እያበሰርን በቀጣይ ተከታታይ ትምህርቶችን በዚህ ቴሌግራም ቻናላችን የምንለቅ መሆኑን በታላቅ ደስታ እንገልጻለን፡፡
አጋፔ የጋብቻና ቤተሰብ የማማከር አገልግሎት