Dr.Gashaw Arega -ዶ/ር ጋሻዉ አረጋ

Dr.Gashaw Arega -ዶ/ር ጋሻዉ አረጋ Health and welbeing awarness

https://youtu.be/xkOl4KrOqvA?si=UrSG9PHVr4x009zCእነሆ!የደም ካንሰርን ምንነት ፣ ምልክቶች እና የህክምና አማራጮች የዳሰስንበት ጥልቅ የፋና-ጤና ፕሮግራም!❤ዶ/ር ...
10/08/2025

https://youtu.be/xkOl4KrOqvA?si=UrSG9PHVr4x009zC

እነሆ!
የደም ካንሰርን ምንነት ፣ ምልክቶች እና የህክምና አማራጮች የዳሰስንበት ጥልቅ የፋና-ጤና ፕሮግራም
!


ዶ/ር ጋሻዉ አረጋ

|

ካንስር ምንድን ነዉ? የካንሰር በሽታ የሚይዘዉ ማንን ነዉ?   [ ክፍል ፩ ]እዉነተኛ የዕለት ከዕለት የዉሎ ገጠመኞች! ፩. ድንቡሽቡሽ ያለ የአራት አመት ልጇን በስስት እያሰበች  'ዶ/ር የ...
02/04/2025

ካንስር ምንድን ነዉ? የካንሰር በሽታ የሚይዘዉ ማንን ነዉ?
[ ክፍል ፩ ]
እዉነተኛ የዕለት ከዕለት የዉሎ ገጠመኞች!

፩. ድንቡሽቡሽ ያለ የአራት አመት ልጇን በስስት እያሰበች 'ዶ/ር የልጄ ህመም ምንድን ነዉ? ንገረኝ 'የደም ካንሰር' ነዉ? ' እዉነት ነዉ? ' መረበሿ ይነበበኛል፤ ድንጋጤዋ ይታየኛል፤ ጭንቀቷ ይገባኛል፤ ህመሟ ይሰማኛል። እንባዎ ይገባኛል።
ስጋት አለ፤ ፍረሃት አለ፤ ጭንቀት አለ፤ ህመም አለ፤
ትጠይቀኛለች፤ አደምጣታለሁ። 'ካንሰር ግን ምንድን ነዉ?' 'ከሳምንት በፊት ይዘል ፡ ይጫወት፡ ይበላ ...ጤናማ የነበረ ልጄ ዛሬ የደም ካንሰር አለበት ስባል እንዴት ልመን?' ትጠይቀኛለች፤
በሀሳቤ የህክምና አማራጮችን እያሰብኩ ፤ ስለ ካንሰር ምንነትም ለማስረዳት ብዕሬን ከነጭ ወረቀት አገናኛለሁ።
፪. ከነገ ዛሬ ደረሰለኝ የሚሉትና ተስፋ የሚያደርጉት የሁለተኛ ደረጃ ትምህርቱን እየተማረ የሚገኘዉ የአይን ብሌኔ ልጃቸዉ የታፋ አጥንቱ (Femur) በማበጡ፡ አጥንት የሚሰብር ህመም እየተሰማ ሲያሰቸግረዉ ቀዬቸዉን ለቀዉ፣ መንገዱን አቋራርጠዉ ወደ እኛ ጋ ለመታከም መምጣታቸዉ ነበር፤ ለእብጠቱ የእግር ምራአይ (MRI) ፡ የበሽታዉን የመሰራጨት ሁኔታ ለማወቅም የሳምባ ሲቲ ስካን (Chest CT scan) አዘዝኩላቸዉ። ናሙና መወሰድም እንዳለበትም ቀስ በቀስ ለማሰረዳት ብሞክርም ንግግሬን አቆርጠዉኝ 'ልጄ ግን ይድናል? የመዳን ተስፋ አለዉ?' በተሸበረ ሰሜት ጠየቁኝ። ከቤተሰብ አንዱም 'ይኼ ነገር ካንሰር ነዉ እንዴ ? 'አለኝ።
፫. ሌሎችም በጣም ብዙ ህፃናትን እናክማለን። ቤተሰቦች በቀጠሮ የክትትል ቀናቸዉ የካንሰር ህክምናቸዉን ያጠናቀቁ ልጆቻቸዉን ይዘዉ ይመጣሉ። ልጆቹም ገና እንዳዩን ሮጠዉ ይጠመጠሙብናል። የቤተሰብ ደስታ....ፈገግታ! ቤተሰቦችም ያሳለፉት የነበረ የህክምና ጊዜን እያሰቡ 'ተመስገን' ሲሉ ይደመጠናል። በህክምና ላይ ላሉ ታካሚዎችና ለአዳዲስ የካንሰር ታካሚዎች ሞራልና ብርታት ይሆኗቸዋል። ከካንሰር ታክሞ መዳን እንደሚቻል ተምሳሌት ይሆናሉ።
ተስፍ አለ፤ መፍትሔ አለ፤ ህክምና አለ ፤ ታክሞ መዳን አለ።
∞∞∞∞∞∞∞∞∞∞∞∞∞∞∞∞∞∞∞∞∞∞∞∞∞∞∞
ለመሆኑ ግን ካንሰር ምንድን ነዉ? የምንወዳቸው ሰዎች በካንሰር መታመማቸዉን ስንሰማ የሚሰማን ምንድን ነዉ? ወደ አዕምሯችን ቀድሞ የሚመጣዉ 'ተስፋ መቁረጥ' ወይንስ 'የህክምና አማራጮች?' ታሚሚዎችስ መታከምን ወይንስ መሞትን ያስባሉ? አብዛኛውን የካንሰር ህመም አይነቶች በጊዜ ከታወቁና ተገቢዉ ህክምና ከተደረገላቸዉ እንደሚድኑስ እናዉቃለን?
∞∞∞∞∞∞∞∞∞∞∞∞∞∞∞∞∞∞∞∞∞∞∞∞∞∞∞∞
ሰዉነታችን የተገነባዉ መሰረታዊ የህይወት ትናንሽ ክፋዮች ከሆኑት ህዋሳት(cells) ነዉ። እነዚሀ ህዋሳት የራሳቸዉ የሆነ ጠባይና የስራ ድርሻ አለባቸዉ። ጤነኛ ህዋሳት ሲያረጁ ወይንም ጉዱት ሲገጥማቸዉ በሌላ ጤነኛ አዲስ ህዋሳት ይተካሉ፤ የተጓዳ ህዋስም ካለ እንዲስተካከል (repair ይደረጋል፤ ይኽም የጤነኛ ህዋሳት መገለጫቸዉ ነዉ።
ህዋሳት የተለመደዉን የጤነኛ ህዋሳት መንገድ መከተል ሲየቅታቸዉ የካንሰር ህመም ይከሰታል። የካንሰር ህዋሳት በሰዉነታቻን ዉስጥ ከቁጥጥር በላይ በሆነ መንገድ የሚራቡ (uncontrolled sustained proliferation) እና የማይሞቱ አዳዲስ ህዋሳትን (replicative immortality ) ፈጥረዉ ይተካሉ። እነዚህም የካንሰር ህዋሳት (cancer cells) እያደጉና እየተራቡ በመምጣት በጤነኛ ህዋሳት ላይ ግፊት በማሳደር (invasion) መጨናነቅን ይፈጥራሉ፤ የማያረጁና የማይሞቱ የካንሰር ህዋሳት (Resisting cell death) በሰዉነት ክፍላችን ይከማቻሉ። ለጤነኛ ህዋሳት የሚያስፈልጉ ንጥረ-ነገሮች፡ የደም አቅረቦት በመሻማት ጤነኛ ህዋሳት በአግባቡ ስራቸዉን ማከናዉን እንዳይችሉ ያደርጓቸዋል። የካንሰር ህዋሳት በጣም እየበዙ ሲሄዱ ወደ ሌሎች የሰዉነት ክፍል ሊሰራጩ (Metastasis) ተጨማሪ ምልክቶችን ይፈጥራሉ። ለምሳሌ የእግር የታፋ አጥንት ካንሰር (Femur Bone sarcoma) ወደ ሳንባ ተሰራጭቶ የትንፍሽ ማጠር ምልክት ፡ የሳምባ ሽፋን ዉኃ/አየር መቋጠር (Hydropneumothorax) ሊያመጣም ይችላል።
∞∞∞∞∞∞∞∞∞∞∞∞∞∞∞∞∞∞∞∞∞∞∞∞∞∞∞∞∞
ካንሰር ዘር፣ ፆታ፣ ቀለም፡ የኑሮ አቅም ሳይለይ በሁሉም የዕድሜ ክልል ዉስጥ (ከህፃናት እስከ አዛዉንት) ያሉ የሚያጠቃ ህመም ነዉ። ካንሰር ከየትኛዉም የሰዉነት ክፍል ሊጀምር ይችላል። የካንሰር አይነቶች ስርጭትም በዕድሜና በፆታ የመለያያት እድል አለዉ። የካንሰር ህዋሳት በሰዉነታችን ዉስጥ የሚያድጉበት እና የሚሰራጩበት መንገድና ፍጥነት የተለያየ ነዉ፤ አንዳንደ የካንሰር አይነቶች በከፍተኛ ፍጥነት የማደግና የመሰራጨት ምልክት ያሳያሉ ፤ ሌሎች ደግሞ በዝግታ የማደገና የመሰራጨት አዝማሚያ ያሳያሉ። በአዋቂዎች ላይ የሳምባ ካንሰር፣ የጡት ካንሰር፣ የማህፀን ካንሰር፣ የአንጀት ካንስር፣ የፕሮስቴት ካንሰር ፣ ከጨጓራና ከገረሮ የሚነሱ ካንሰር ሊከሰቱ ይችላሉ። በህፃናትና በልጆች የሚከሰቱ ዋና ዋና የካንሰር አይነቶቸ በቅደም ተከተላቸዉ የደም ካንስር (Acute Leukemia)፣ የጭንቅላትና የህብለሰረሰር ዕጢዎች (Central Nervous Tumors)፣ የንፍፊት ዕጢ/ካንሰር(Lymphoma)፣ ኒዮሮብላስቶማ፣ የኩላሊት ካንሰር ፤ የአጥንት ካንሰር....ወ.ዘ.ተ ናቸዉ።
∞∞∞∞∞∞∞∞∞∞∞∞∞∞∞∞∞∞∞∞∞∞∞∞∞
አብዛኞቹ የካንሰር አይነቶች እንደ እባጭ ያለ የሚያድ ዕጢ ይሰራሉ፤ ይሁንና ሁሉም ዕጢ/ዕባጭ ካንሰር ናቸዉ ማለት አይደለም። ካንሰር ያልሆኑ እጢዎች ምኝ ዕጢ (Benign tumor) ይበላሉ፤ የካንሰር ህዋሳትንና መገለጫዎችን የያዙ ዕጢዎች ከባድና አደገኛ እጢዎች (Malignant tumors) ይባላሉ። ምኝ ዕጢን ከከባድ አደገኛ እጢ ለመለየትም ከራዲዮሎጂ ምርመራ በተጨማሪ ናሙና ወስዶ እጢዉን መመርመር ያስፈልጋል።
ነገር ግን እንደ የደም ካንሰር (Leukemias) ያሉ የካንሰር ህመሞች በደም ህዋሳት አማካኝነት ወደ ተለያዩ የሰዉነት ክፍሎች ይሰራጫሉ እንጂ እብጠት/እጢ አይሰሩም።
∞∞∞∞∞∞∞∞∞∞∞∞∞∞∞∞∞∞∞∞∞∞∞∞∞∞
በቀጣይ ክፍል [ክፍል ፪] ካንሰር ከምን ይመጣል? የተለመዱ የካንሰር ህመም ምልክቶች ምንድን ናቸዉ? የሚለዉን እናያለን።

በቸር ያቆዬን።

ዶ/ር ጋሻዉ አረጋ
የህፃናት ሕክምናና የልጆች ጤንነት ስፔሻሊስት
የደምና ተዛማጅ ህመሞች፤ የካንሰር ሰብ-ስፔሻሊስት

በ5 ክልሎች እና በ2 የከተማ አስተዳደሮች ኤች አይ ቪ/ኤድስ በወረርሽኝ ደረጃ ላይ እንደሚገኝ ተገለጸ። (አብመድ)  ክልሎች እና በ2 የከተማ አስተዳድሮች ኤች አይ ቪ/ኤድስ በወረርሽኝ ደረጃ...
19/02/2021

በ5 ክልሎች እና በ2 የከተማ አስተዳደሮች ኤች አይ ቪ/ኤድስ በወረርሽኝ ደረጃ ላይ እንደሚገኝ ተገለጸ።
(አብመድ)
ክልሎች እና በ2 የከተማ አስተዳድሮች ኤች አይ ቪ/ኤድስ በወረርሽኝ ደረጃ ላይ እንደሚገኝ የፌዴራል የኤች አይ ቪ/ኤድስ መከላከያና መቆጣጠሪያ ጽሕፈት ቤት አስታወቀ።
እንደ ሀገር የስርጭት መጠኑ በወረርሽኝ ደረጃ ባይሆንም በጋምቤላ፣ አማራ፣ ሀረሪ፣ አፋር እና ትግራይ ክልሎች፣ እንዲሁም በአዲስ አበባ እና ድሬዳዋ የከተማ አስተዳደሮች ላይ የስርጭት ምጣኔው ከአንድ በመቶ በላይ በመሆኑ በወረርሽኝ ደረጃ እንደሚገኙ የፌዴራል የኤች አይ ቪ/ኤድስ መከላከያና መቆጣጠሪያ ጽሕፈት ቤት የህዝብ ግንኙነት እና ኮሚዩኒኬሽን ዳይሬክተር አቶ ዳንኤል በትረ በተለይ ለኢቲቪ ተናግረዋል።
በሀገር ደረጃ የኤች አይ ቪ/ኤድስ በወረርሽኝ ደረጃ ከፍተኛ የስርጭት መጠን ያለባቸው በጋምቤላ 4. ነጥብ 6 በመቶ፣ በአዲስ አበባ 3 ነጥብ 4 በመቶ፣ በድሬዳዋ 2 ነጥብ 5 በመቶ፣ ሀረሪ 2 ነጥብ 4 በመቶ፣ በአፋር 1 ነጥብ 4 በመቶ፣ በትግራይ 1. ነጥብ 2 በመቶ፣ በአማራ 1 ነጥብ 2 በመቶ ደረጃ ላይ ይገኛሉ ብለዋል አቶ ዳንኤል።
በዓለም ጤና ድርጅት መረጃ መሰረት አንድ በሽታ ወረርሽኝ ነው የሚባለው የስርጭት ምጣኔው አንድ በመቶ እና ከዚያ በላይ ሲሆን፣ እንደ ሀገር የኤች አይ ቪ/ኤድስ የስርጭት መጠን 0.93 በመቶ ስለሆነ በወረርሽኝ ደረጃ አይደለንም ሲሉ አቶ ዳንኤል ገልጸዋል።
የኤች አይ ቪ ኤድስ በገጠር፣ በከተሞች እንዲሁም በተለያዩ በማህበረሰብ ክፍሎች ዘንድ የተለያየ ዓይነት የስርጭት ምጣኔ እንዳለው ተገልጿል።
በማህበረሰብ ደረጃ ከፍተኛ የስርጭት ምጣኔ የሚታይባቸው ሴተኛ አዳሪዎች ሲሆን ቁጥሩም 23 በመቶ ነው ተብሏል።
በመቀጠልም፣ ባሎቻቸውን በሞት ያጡ ሴቶች ላይ 19 በመቶ ሆኖ ይታያል ብለዋል አቶ ዳንኤል።
የረጅም ርቀት አሽከርካሪዎች፣ ኮንስትራክሽን ሳይት ላይ የሚሰሩ ሰራተኞች፣ አፍላ ወጣቶች ላይ ከ2 በመቶ በላይ የስርጭት ምጣኔ ያሳያል ሲሉ አቶ ዳንኤል ተናግረዋል።
በከተማ ያለው የስርጭት ምጣኔ 3 በመቶ ሲሆን በገጠር ያለው ደግሞ 0.4 ደርሷል ተብሏል።
በተጨማሪም በወንዶች ያለው የስርጭት ምጣኔ ከሴቶች ይልቅ ዝቅ ብሎ እንደሚገኝ ተገልጿል፡፡
የኤች አይ ቪ የስርጭት ምጣኔ 61 በመቶ የሚሸፍኑት ሴቶች ሲሆኑ፣ 39 በመቶ የሚሆነውን የሚሸፍኑት ወንዶች እንደሆኑ አቶ ዳንኤል ተናግረዋል።
የኤች አይ ቪ/ኤድስ መከላከል ዙሪያ ዘርፈ ብዙ ምላሽ የሚጠይቅ ስለሆነ ሁሉም የማህበረሰብ ክፍል ኃላፊነቱን በአግባቡ ሲወጣ የስርጭት ምጣኔው መቀነስ ላይ ውጤታማ መሆን ይቻላል ሲሉ የኮሙኒኬሽን ዳይሬክተሩ መናገራቸውን የዘገበው ኢብኮ ነው።

መልካም ነዉ!
19/02/2021

መልካም ነዉ!

"የአሁኑ ትውልድ ፈተና : Retinopathy of Prematurity"በዶ/ር ሳዲቅ ታጁ የህጻናት ዓይን ህክምና ሰብስፔሻሊስትከሁለት አስርት አመታት በላይ በትዳር ለኖሩት ወ/ሮ ለታይና አቶ ...
16/02/2021

"የአሁኑ ትውልድ ፈተና : Retinopathy of Prematurity"
በዶ/ር ሳዲቅ ታጁ የህጻናት ዓይን ህክምና ሰብስፔሻሊስት
ከሁለት አስርት አመታት በላይ በትዳር ለኖሩት ወ/ሮ ለታይና አቶ ገ/እግዚ (ለዚህ ጽሁፍ ሲባል ስማቸው የተቀየረ) ትዳራቸው በልጅ አለመባረኩ ህይወታቸውን አክብዶታል፡፡
ኑሮአቸውን ከመቐለ በስተደቡብ 60ኪ.ሜ እርቃ በምትገኘው ሳምሪ አቅራቢያ ያደረጉት እነዚህ ባለትዳሮት ኑሮዋቸውን በግብርና የሚገፉ ኑሮ ከእጅ ወደ አፍ የሆነባቸው ግና ጭንቀታችው የኑሮ ውጣውረድ ሳይሆን የዘወትር ፀሎትና ስለታቸው፤ ጎጆቸው በልጆች ጫጫታና ሩጫ እንዲደምቅላቸው ነበረ፡፡
ምንም እንኩዋን የወ/ሮ ለታይ እድሜ ወደ አርባዎቹ መጨረሻ እየገሰገሰ እርጅናም መጣሁ መጣሁ ቢልም በፈጣሪያቸው በነበራቸው መታመን አንድ ቀን የአብራካችንን ክፍያ እንስማለን የሚከው ምኞታቸው ለአንድ አፍታም ደብዝዞ አያውቅም፡፡ በትዳር መካከል የአብራክ ክፍያ ልጅ አለመኖር እንደትልቅ እንከን በሚቆጥር ማህበረሰብ ውስጥ እነዚህ ጥንዶች በታማኝነት መኖራቸው አንድም አንዳቸው ለሌላቸውያላቸውን ፍቅር በሌላ መልኩም አምላካቸው ላይ ያላቸውን መተማመን ያሳያል፡፡
ወ/ሮ ለታይ ነፍሰጡር መሆናቸውን ያወቁት የሆዳቸው መግፋት ካጤኑ በኃላ ጤና ተቋም ሄደው በደረጉት ምርመራ ነበር፡፡ በአቅራቢያቸው የሚገኙ የጤና ባለሞያዎች ከእድሜያቸው መግፋት ጋር ተያይዞሊኖሩ የሚችሉ ችግሮችን ከግምት በማስገባት የወሊድ ክትትላቸውን ከመኖሪያቸው 60 ኪ.ሜ በሚርቀው መቐለ ከተማ በሚገኘው በአይደር ስፔሻላይዝድ ሆስፒታል እንዲያደርጉ ይመከራሉ፡፡
በባለሞያዎቹ ምክር ወደ አይደር ስፔሻላይዝድ ሆስፒታል ያቀኑት ጥንዶቹ በተደረገላቸው ምርመራ ወ/ሮ ለታይ በአንድ ጊዜ ሶስት ልጆች እንደፀነሱ ሲነገራቸው ደስታቸውን በለቅሶና በምስጋና ለፈጣሪያቸው አደረሱ፡፡ “የታገሰ ከሚስቱ ይወልዳል” የሚለው ብሂል እነሱ ላይ ደርሶ ሲያዩት ያሳለፉት የትካዜና የባዶነት አመታት በደማቅና በተስፋ በተሞሉ የእርግዝና ወራት ተተኩ ፤ ምስጋና ለእናቶችና ለህፃናት ህክምና ልዩ ትኩረት ለሰጠው የጠና ፖሊሲ ፤ እሱን ተከትሎ ተግባራዊ ለሆነው የህክምና ትስስር (Referral System) እና ለአይደር ስፔሻላይዝድ ሆስፒታል ሃኪሞች ይሁንና ወ/ሮ ለታይ ሶስት ልጆችን በአንድ ጊዜ በሰላም ተገላገሉ፡፡
ሆኖም ወ/ሮ ለታይ ከቀናቸው በፊት (ከዘጠኝ ወር በፊት) የወለዱ በመሆኑ እንዲሁም ሁሉም ልጆቻቸው ከአንድ ኪሎ በታች ሆነው የተወለዱ በመሆኑ በሆስፒታሉ ሙቀት ክፍል ውስጥ (Neonatal intensive care unit NICU ) እንዲቆዩ ተደረጉ፡፡
በሆሲፒታሉ የህፃናት ስፔሻሊስት ሃኪሞች/ ነርሶች ያላሰለሰ ጥረት ለሁለት ወራት በክፍሉ ከታከሙ በኃላ የልጆቹ ጤናቸው ሁኔታ በጣም በመሻሻሉ ከነሙሉ ጤናቸው ወደቤታቸው ተሸኙ፡፡ ጥንዶቹም ሁለት ሆነው ወጥተው አምስት ሆነው ወደ መኖሪያ ቄያቸው ተመለሱ፡፡
ከሁለቱ የለሆሳስ ንግግር በቀር ጭር ብሉ የነበረው ደሳሳ ጉጆቸው በማያቋርጥ የጨቅላ ህፃናት ለቅሶና ጫጫታ ተሞላ፡፡ በአንድ ጊዜ የሶስት ህፃናት የማያቋርጥ ለቅሶ ከባድ እንደሆነ ማንም ሊገምተው ይችላል፡፡ ይሁንና ለነወ/ሮ ለታይ እንደ ትንግርት ነበረ፡፡
የወ/ሮ ለታይ የበዛ ትኩረት የልጆቻቸውን የእይታ ሁኔታ እንደጠበቁት አልሆን አላቸው እሳቸው ቀን ከሌት አይናቸው ለሶስቱም ልጆቻቸው መንቀል ቢያዳግታቸውም ህፃናቱ በተራችው ዓይናቸውን በደንብ እያዩቸው እየተከተሉቸው እንዳልሆነ ገባቸው፡፡
ሁኔታውን ሊጠይቋቸው ለመጡ ጎረቤትና ዘመድ ቢናገሩም ‘’እንዴ ተያቸው ገና ጨቅላ ህፃናት ናቸው’’ የሚል ምላሽ በማግኘታቸው ለጊዜው ‘’እፎይ’’ አሉ:: ይሁንና ይህ ንቁ የሆነ ምልከታቸው በቀጣይ ሁለት ሳምንታት ሶስቱም ልጆቻቸው ጥቁሩ የዓይን ክፍል (ብርሃን ፊ) ነጭ ነገር እንደጣለባቸው አስተዋሉ፡፡
ሁኔታው እንቅልፍ ቢነሳቸው በአቅራቢያቸው ወዳለ ጤና ጣቢያ ቢሄዱም ይህ ነው የሚባል መፍትሄ ሊያገኙ አልቻሉም፡፡ ‘’የምሽት አልማዛቸው’’ ሁኔታ ያሳሰባቸው ወላጆች በሰላም ወዳገላገለቸው የአይደር ስፔሻላይዝድ ሆስፒታልይዘው ሄዱ፡፡ ወላጆቹ የልጆቻቸው የዓይን የችግሩ ግዝፈት የገባቸው የሆስፒታሉ ሃኪሞች ለተሸለ ህክምና ወደ ዳግማዊ ሚኒሊክ ሆስፒታል (አዲስ አበባ) መሄድ እንዳለባቸው ሲነገራቸው ነው፡፡
እንደሙሉ ጨረቃ ፈክቶ የነበረው የነበረው ህይወታቸው በአንድ ጊዜ በስጋትና ጭንቀት ተወጠረ፡፡ አዲስ አበባ በምናችን እንሄዳለን? እዛስ ምን ይጠብቀናል? የልጆቻችንስ የዓይን ጤና መጨረሻ ምን ይሆናል? ፈጣሪስ ለምን አብዝቶ ፈተነን? የማያልቁ ጥያቄዎችና ጭንቀት……
የቤተሰቡን ጭንቀት የተረዳው ጎረቤትና ዘመድ አዘማድ በኢትዮጵያውያን የመረዳደት ስሜት ቤተሰቡን በማገዙ ወደ ዳግማዊ ሚኒሊክ ሆስፒታል (አዲስ አበባ) አቀኑ፡፡..
እነዚህን የህይወት ውጣ ውረድ ፤ የምኞት ፤ የደስታ ፤ የጭንቀት ጊዚያትን ያሳለፉ ህይወታቸው በተስፋ ፤ በደስታ ፤ በጭንቀት የተሞላባቸው የመጡበት የቦታ እርቀት ፤ እድሜና የኑሮ ሁኔታ የደከመው ፤ ሶስት ደሳስ የሚሉ ጨቅላ ህፃናትን ከሬዚደንት ሃኪሞች ጋር አብሬ አየሁኃቸው፡፡
የሶስቱንም ህፃናት ዓይን በጥልቀት መርምረን ችግሩን ለየን፡፡ አዘንኩ በጣም አዘንኩም እኔም ከሬዚደንት ሃኪሞች ፊትለፊት በማምሻ እድሜቸው በሶስት ልጆች በተባረኩ ጎልማሳ ወላጆች ፊት የመልካም የተስፋ ዜና ብስራትን የሚጠብቁት ዓይኖች እንዲሁም በተስፋ የህፃናት ዓይን ህክምና ላይ እንደሚሰራ ሃኪም ጥሩም መጥፎም ዜና ለወላጆች ስነግር ኖሬያለሁ፡፡
ዛሬ ከበደኝ ! ሰው መሆን አማረኝ ራሴን በእነሱ ጫማ ውስጥ መጨመር! እኔ ብሆን ምን ይሰማኛል? የሶስቱም የዓይን ብርሃን የሚቀበሉ ግርግዳ ከጨቅላነታቸው ጋር ተያይ በሚመጣ ችግር ተላቀዋል፡፡ አሁን ባለበት ደረጃ መታከም አይችልም፡፡ ዘግይታችኃል ፤ በመጨረሻ እድሜችሁ ያገኝችኃቸው ልጆች ሁሉም ዓይነስውር ሆነው ይኖራሉ! ለመናገር ከበደኝ ቁጭ አልኩና አወራኃቸው ማናቸው? ስለኑሮአቸው እንደህመምተኛ ሳይሆን እንደጓደኛ (ቤተሰብ) አወራኃቸው፡፡ ከላይ የፃፍኩትን ታሪክ ነገሩኝ፡፡
ባለቅኔው ‘’ወንድ ልጅ እንዴት ያለቅሳል’’ ነበር ያለው? ወደ ውስጤ አነባሁ፡፡ የማይቀረውን መርዶ ባረዳኃቸው ወቅት የወላጆቹ በተለይ ወ/ሮ ለታይ ሀዘን ለቅሶ ዋይታ ስው ከሞተበት በላይ ነበር ፡፡
ይህ ከሆነ ሁለት አመት ሞላው፡፡ አሁን ለምን ፃፍኩት?
ገፊው ምክንያት “አንድ መልካም ያልሆነ ድርጊት ስታይ በእጅህ አስቁም ወይም ተናገር” በሚል ሀይማኖታዊ ምክር ምክንያት ነው፡፡
ለዚህ ጽሁፍ መነሻ የሆነኝ ሰሞኑን በመዲናችን አዲስ አበባ በምክትል ከንቲባዋ የተመረቀው የእናቶችና ህፃናት ሆስፒል ነው፡፡ መንግስታችን ላለፉት አስር አመታት ገደማ የእናቶችና ህፃናት ህክምና ላይ ከፍተኛ ትኩረት በመስጠት በሺዎች የሚቆጠሩ የእናቶችና ህፃናትን ህይወት ለመታደግ ችሏል፡፡ ከፌደራል ጤና ሚኒስቴር አንስቶ ጤና ኬላ ድረስ ለዘርፉ በተሰጠው ትልቅ ትኩረት ትርጉም ያለው ለውጥ መጥቷል፡፡ የጨቅላ ህፃናት ሞት ከእጥፍ በላይ ቀንሷል፡፡ ይህ እጅግ በጣም የምኮራበት ተግባር ነው፡፡
ታሪካዊ ዳራ
የአለማችን የጤና ታሪክ በምናጠናበት ወቅት የእናቶችና ህፃናትን የጤና አገልግሎት መሻሻል ጋር ተያይዞ በተለይም የጨቅላ ህፃናት ጤና አገልግሎት ከማሳለጥ ጋር በተገኛኘ ሆስፒታሎች የሙቀት ክፍል (Neonatal intensive care unit-NICU) ይገነባሉ፤ የጤና ባለሞያዎቹም በዘርፉ ይሰለጥናሉ፡፡
በመሆኑም ከቀናቸው በፊት የሚወለዱ ጨቅላ ህፃናት የክብደት መጠናቸው በጣም የቀነሰና ተጓዳኝ የጤና ችግሮች ላሏቸው ህፃናት በሚደደረግላቸው እንክብካቤ በህይወት የመኖር ስፋ ይኖራቸዋል፡፡
ከ1920-30ዎቹ ባደጉት ሀገራት የተቀጣጠለው ይህ የአለም የጤና አብዮት በመቶ ሚሊዮን የሚቆጠሩ የእናቶችና ህፃናትን ህይወት ታድጎል፡፡ ይሁንና ይህንን የጤና አብዮት ተከትሎ በአውሮፓ እና ስሜን አሜሪካ መጀመርያ ክ1940-50 እ.አ.አ ቀጥሎም ከ1970-80 እ.አ.አ ሀገራቱ በየዓይነ ስውርነት ወረርሽኝ ተጥለቀለቁ፡፡ አለማችን ከፍተኛዉን የህፃናት የዓይነ ስውርነት አስተናገደች፡፡
በወርሃ ግንቦት 19650 እ.አ.አ የተወለደው ታዋቂው ጥቁር አሜሪካዊ ዘፋኝም Stevie Wonder የዚሁ በሽታ ተጠቂ ነበር፡፡ የጊዜዉ አዲስ በሽታ Retinopathy of Prematurity (ROP)- ከጨቅላነት ጋር በተያያዘ የብርሃን መቀበያ የደም ስሮች መቀንጨር የሚል ስያሜ ተሰጠው፡፡
ROP ምንድነው (ከጨቅላ ህፃናት ጋር በተያያዘ የብርሃን ተቀበይ የደም ስሮች መቀንጨር)
ብርሃን የሚቀበለው የዓይን ክፍል(Retina) ያሉ የደም ስሮች እድገታቸው በአግባቡ አጠናቀው መላውን ብርሃን ተቀባይ ክፍል ለመሸፈን ፅንሱ የ9 ወራት ቆይታውን በእናቱ ማህፅን መቆየት ይኖርበታል፡፡ በእናት ወደ ፅንሱ የሚተላለፉ ሆርሞኖችና ኦክጂን በብርሀን ተቀባይ የደም ስሮች ለመፈጠር ወሳኝ ናቸው፡
በመሆኑም ከግዜያቸው ቀደም ብለው የሚወለዱ ጨቅላ ህፃናት ብርሀን ተቀባይ የደም ስሮቻቸው መላውን ብርሀን ተቀባይ የዓይን ክፍል(Retina) ሳይሸፍኑ ይቀራሉ፡፡ ጨቅላ ህፃናቱ ህይወታቸውን ለማትረፍ ሙቀት (Neonatal intensive care unit NICU) ይቆያሉ፡፡
በጤና ባለሞያዎች ያላሰለሰ ክትትል፤ በሚሰጣቸው የኦክጂንና ሌሎች አስፈላጊ ህክምናዎች ህይወታቸውን ማትረፍ ይቻላል፡፡ ይሁንና በደም ስር ያልደረጀው ብርሀን ተቀባይ የዓይን ክፍል(Retina) ተፈጥሮያዊ ባልሆኑ አዳዲስ የደም ስሮች( New Vessels) ይወረራሉ፡፡ ተፈጥሮያዊ ባልሆኑ አዳዲስ የደም ስሮች( New Vessels) በቀላሉ ይደማሉ ችግሮቹ ታይተው በወቅቱ ካልታከሙ ብርሀን ተቀባይ የዓይን ክፍል(Retina) እንዲላቀቅ (Retinal Detachment) ሊዳርጉ በሂደትም ዓይነ ስውርነት ይዳርጋሉ፡፡
እንግዲህ ባጭሩ Retinopathy of Prematurity(ROP) ከጨቅላነት ጋር የተያያዘ የብርሃን መቀበያ የደም ስሮች መቀንጨር ማለትይህ ነው፡፡
ከላይ እንደገለጽኩት በሙቀት ክፍል (Neonatal intensive care unit) በሚሰጠው ክትትልና ህክምና ምስጋና ለጤና ባለሞያዎች ይሁንና እነዚህ ጨቅላ ህፃናት ህይወታቸው ለመታደግ ተችሏል፡፡ በዚህም መንግስትም የጤና ባለሞያዎችም ባደረጉት ጥረት የሚያኮራ ውጤት ተገኝቷል፡፡
ይሁንና Retinopathy of Prematurity(ROP) ከጨቅላነት ጋር የተያያዘ የብርሃን መቀበያ የደም ስሮች መቀንጨር በቂ እውቀት ግንዛቤ ስለሌለ አሁን አሁን Retinopathy of Prematurity (ROP) ምክንያት ህይወታቸው ተርፎ የዓይነ ብርሀናቸውን የሚያጡ ጨቅላ ህፃናት ቁጥር እየጨመረ ነው ፡፡ ከ80 አመት በፊት የተፈጠረ ክስተትን ያልጠየቀ ህዝብና መንግስት “3ኛውን የዓይነ ስውርነት ወረርሽኝ” ለማስተናገድ መንገዱን ተያይዘውታል፡፡
የROP ከጨቅላ ህፃናት ጋር በተያያዘ የብርሃን ተቀበይ የደም ስሮች መቀንጨር) አጋላጭ ምክንያቶች ምንድን ናችው?
• ከቀኑ ቀድሞ መወለድ (በተለይ ከ 34 ሳምንት እርግዝና በፊት መወለድ
- የውልደት ክብደት መጠን ማነስ ( ከ2500 ግራም በታች መሆን
- ተያያዥ የጤና እከሎች የሳምባ በሽታ… ለዚህም ሲባል የኦክጂን ህክምና መውሰድ
ሌሎችም ምክንያቶች ተጠቃሽ ናቸው ፡፡
ምን ይደረግ ?
ያደጉ ሀገራት ክ1940-50 እ.አ.አ ቀጥሎም ከ1970-80 እ.አ.አ ካጋጠማቸው የህፃናት ዓይነ ስውርነት ማዕበል በኃላ በሙቀት ክፍሎቻቸው (Neonatal intensive care unit) ከሚሰጠው የጨቅላ ህክምና ጋር ተያይዞ የROP ልየታ (ROP Screening) አንዱ የህክምናው ክፍል አድርግዋለ፡፡
ባደጉ ሃገራት ሙቀት ክፍል (Neonatal intensive care unit) ያላቸው የጤና ተቋማት የዓይን ምርመራን ግድ ያደርጋሉ፡፡ የነዚህ ጨቅላ ህፃናት ብርሃን የሚቀበለው የዓይን ክፍል ቀደም ብሎ የበሽታው ምልክት ከታየ በኃላ በሚደረጉ ህክምናዎች በቀለሉ በህፃናቱ ላይ የሚከሰቱ ዓይነ ስውርነት መከላከል ይቻላል፡፡

በሃገራችን አሁን ባለው ሁኔታ በጥቂት ተቋማት (ጥቁር አንበሳ ፤ ዳ/ሚኒሊክ እና የተወሰኑ የግል ተቋማት) በቀር ህክምናው እየተሠጠ አይደለም፡፡
በአዲስ አበባ የኒቨርሲቲ በቅርቡ እኔ በመራሁት ጥናት ጥቁር አንበሳ ፤ ዳ/ሚኒሊክ ሙቀት ክፍል (NICU) ተኝተው ህክምና ሲየገኙ ከነበሩ ጨቅላ ህፃናት መሃከል 48% (መጠኑ ቢለያይም) ROP ነበረባቸው፡፡ ከነዚህ ውስጥ ችግሩ ያለባቸው በጊዝው በመታየታቸው ብሃናቸውን መታደገ ተችሏል፡፡
በእኔ እይታ ባደገ /መሰለጠነ ሃገር /ማህበረሰብ ሴቶችና ህፃናት ከፍ ብለው ይታያሉ፡፡ በዚህም አኳያ በቅርቡ የተመረቀው የህፃናትና እናቶች ሆስፒታል የህፃናትና ሴቶችን ጤና ከፍ ከማድረግ አካያ የሚኖረው ድርሻ በጉልህ ሊታይ የሚችል ነው፡፡
ይሁንና ከሌሎች ሃገራት ተምረን የህፃናትን የሞት የመቀነስ ግቦች የህፃናት ዓይንን ታሳቢ ካለደረግን በቀጣዩ ትውልድ እንዲሁም በሃገር ላይም ትልቅ ችግር ማኖራችን አይቀርም፡፡ሀሉም የህፃናት የጤና ግቦች ፤ ጤናማ ውጤታማ አምራች ትውልድን አሻግረን ማየት አለብን፡፡ የወ/ሮ ለታይ አይነት አሳዛኝ ታሪክ ሁሉም ሊማርበት ይገባል፡፡ ክቡር ህይወትን አትርፎ የነፃነት ቀንዲል ለመሆነ የሰውነት ክፍል (እይታ) ግድ የለሽነት ተገቢ አይደለም፡፡ አዲሱን ሆስፒታል ጨምሮ የሙቀት ክፍል ያላቸው የጤና ተቋማት በሙሉ የህፃናት ዓይን ህክምና አገልግሎት አሰጣጡ አንዱ ክፍል ሊሆን ይገባል፡፡
.
እኔና ባልደረቦቼ አሁንም በየቀኑ የወ/ሮ ለታይ እይነት ታሪከ ያገጥመናል፡፡ የመወሰን ስልጣን ያለችሁ ሰዎች ምክራችንን ስሙ!!
እይታ የነፃነት ቀንዲል ነው፤ህይወት ሰጥተን ብርሀን አንንፈግ!!

እንኳን ደስ አላችሁ!! ስለ አገልግሎታችሁ እናመሰግናለን ።!!ዓለም አቀፍ የጋይናኮሎጂ ካንሰር ማኅበር ( International Gynecologic Cancer Society) በዓለም አቀፍ ፕሮ...
13/02/2021

እንኳን ደስ አላችሁ!! ስለ አገልግሎታችሁ እናመሰግናለን ።!!

ዓለም አቀፍ የጋይናኮሎጂ ካንሰር ማኅበር ( International Gynecologic Cancer Society) በዓለም አቀፍ ፕሮግራሙ በዚህ ሳምንት በዓለም ዙሪያ ካስመረቃቸውን አምስት ሰብስፔሻሊስት ሐኪሞች ውስጥ ሁለቱ ኢትዮጵያውያን መሆናቸውን ትናንት በድረገጹ ላይ ባስነበበው "የእንኳን ደስ ያላችሁ" መልእክቱ አስታውቋል።

ሁለቱ ኢትዮጵያውያን ሐኪሞች የቅዱስ ጳውሎስ ሚሊነየም ሕክምና ኮሌጅ ባልደረባ የሆኑት ረዳት ፕሮፌሰር ዶ/ር ቤቴል ደረጀ እና የአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ በጥቁር አንበሳ ሆስፒታል የፅንስና ማህፀን ስብ ስፔሻሊስት ባልደረባ የሆኑት ረዳት ፕሮፌሰር ዶ/ር ዳዊት ወርቁ መሆናቸው ታውቋል።

ይህ ለሀገራችን ኢትዮጵያም ሆነ ለሕክምና ኮሌጆቹ በዘርፉ ያለብንን የሰለጠነ ባለሙያ እጥረት ለማቃለል ስለሚያግዝ ለኢትዮጵያችን መልካም ዜና ነው።

ምንጭ- የቅዱስ ሆስፒታል ሚሊኒየም ሕክምና ገፅ

12/02/2021

ማስታወቂያ!!!
በጭንቅላት ውስጥ አላስፈላጊ ውሃ መጨመር( Hydrocephalus ) እና የጀርባ የአፈጣጠር ችግር (spina bifida)ችግር ያለባቸውን ሕጻናት ከየካቲት 9 ቀን ጀምሮ ነጻ ህክምና ይሰጣል፡፡
ስለዚህ ወላጆች ልጆቻችሁን 976 በመደወል አንድታስመዘግቡ በማክበር እንጠይቃለን፡፡

የቅዱስ ጳውሎስ ሆስፒታል ሚሊኒየም ሕክምና ኮሌጅ

11/02/2021

ማሳሰቢያ

የ2012 ዓ ም የ12ኛ ክፍል ማጠናቀቂያ ብሄራዊ ከዚህ ቀደም ይሠጥበት በነበረው የአፈታተን ስነ- ስርዓት ፈተናው ከየካቲት 29 እስከ መጋቢት 2 /2013 ዓ ም ድረስ ፈተናው ይሠጣል ።

የት/ሚ/ር ህ/ግንኙነት ዳይሬክተር

(ሰምተን እናሰማ)

በአዲስ አበባ በ700 ሚሊየን ብር የተገነባው የእናቶችና ህፃናት ሆስፒታል ግንባታ መጠናቀቁ ተገለጸ******************(ኢ ፕ ድ )በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር በ700 ሚሊየን ብር...
09/02/2021

በአዲስ አበባ በ700 ሚሊየን ብር የተገነባው የእናቶችና ህፃናት ሆስፒታል ግንባታ መጠናቀቁ ተገለጸ
******************
(ኢ ፕ ድ )

በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር በ700 ሚሊየን ብር የተገነባውና በሀገራችን የመጀመሪያው ትልቁና ዘመናዊ የእናቶችና ህፃናት ሆስፒታል መጠናቀቁ ተገለጸ።

የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር በጤናው ዘርፍ በተለይ በወሊድ እና ተያያዥ ጉዳዮች በእናቶችና ህጻናት የሚደርሰውን የሞት ምጣኔ ለመቀነስ በአይነቱ በኢትዮጵያ የመጀመሪያ የሆነና ደረጃውን የጠበቀ የእናቶችና ህጻናት ሆስፒታል ተጠናቆ
የካቲት 4, 2013 ምክትል ከንቲባ ወ/ሮ አዳነች አቤቤ ይመረቃል።

በተመሳሳይ ሰአት ለ7 እናቶች የኦፕራሲዮን አገልግሎት መስጠት የሚያስችል ሆስፒታል ነው። ወረቀት አልባ አገልግሎት የሚሰጠው ሆስፒታሉ ዘመናዊ የህክምና ቁሳቁሶች ተሟልተውለታል።

ግንባታው ቀድሞ ለመለስ ዜናዊ አመራር አካዳሚ ተብሎ የተጀመረ ሲሆን የከተማ አስተዳደሩም ካቢኔ በከተማችን ትልቅ የአገልግሎት ችግር ያለበትን የእናቶችና ህጻናት ጤና ቅድሚያ በመስጠት ሰባት መቶ ሚሊየን ብር በመመደብ ተጨማሪ ግንባታ በማድረግ እና ነባሩን ግንባታ በማሻሻል ወደ ሆስፒታልነት እንዲቀየር መደረጉን ከአዲስ አበባ ከተማ ፕሬስ ሴክሬታሪያት ያገኘነው መረጀ ያመለክታል።

መልካም ዜና ለአዲስ አበባ አና አካባቢው ነዋሪዎች # Share  # Share  # Shareየአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ፣ የአይን ህክምና ክፍል በዳግማዊ ምንሊክ ሆስፒታል ነፃ የአይን ሞራ ግርዶሽ...
09/02/2021

መልካም ዜና ለአዲስ አበባ አና አካባቢው ነዋሪዎች
# Share # Share # Share
የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ፣ የአይን ህክምና ክፍል በዳግማዊ ምንሊክ ሆስፒታል ነፃ የአይን ሞራ ግርዶሽ የቀዶ ህክምና አገልግሎት በስፔሻሊስት ሀኪሞች ለመስጠት ተዘጋጅቷል። ስልሆነም ማንኛውም የአይታ ችግር ያለበት ሰው በ የካቲት 21 ቀን 2013 ዓ.ም በዳግማዊ ምንሊክ ሆስፒታል በመገኘት አና ምርመራ በማድረግ የእገልገሎቱ ተጠቃሚ መሆን ይችላሉ።
!
Good News!
The Department of Ophthalmology, Addis Ababa University has organized a free cataract surgery for those in need at Menelik II hospital! Anyone who has visual reduction attributable to cataract can come and be screened on February 28, 2021, at Menelik II hospital for subsequent cataract surgery!
!

ODUU AAGAA!
UUMMATA FINFINNEE FI NAANNAWAA ISHII MARAAF
HOSPITAALLI RIFERAALAA MINILIK NAMOOTA DHIBEE MOORA IJAATIIN RAKKOO ARGUUTIIF SAAXILAMANIIF TAJAAJILA BAQAQSANII YAALUU TOLAAN KENNUUF OGEESSOTA OLAANOO HOSPITAALICHAA QABATEE ISIN EEGA
KANAAFUU NAMOOTNI RAKKOO MOORA IJAA QABDAN HUNDI GUYYAA GAAFA 21/06/2013 MOORAA HOSPITAALICHAATTI ARGAMTANII QORATAMUUN TAJAAJILA KANA TOLA ARGACHUU AKKA DANDEESSAN GAMMACHUUDHAAN ISINIIF IBSA
YUUNIVARSIITII FINFINNEETTI KUTAA YAALA

የአዲስ አበባ ዩኒበርስቲ የአይን ህክምና

07/02/2021

ከሶስት ወራት በፊት በኮሮና የህክምና ማዕከል ለአንድ ወር ለኮሮና ታካሚ ህፃናት ሙያዊ አገልግሎት የመስጠት እድሉ ነበረኝ። በቆይታዬም ወደ ስምንት ህፃናትን ለማከም ችለን ነበር። ዛሬ የሰማሁት ነገር ግን ከመቼዉም በላይ አስደንግጦኛል። በአንደ ጀምበር ብቻ አምስት ኦክሲጂን የሚያስፈልጋቸዉና ክትትል የሚሹ ህፃናት ወደ ኮሮና ማገገሚያ ማዕከል መግባታቸዉን አስተዉያለሁ። በዚያ ላይ የኮሮና ታካሚዎች ቁጥር እያሻበቀ በመሆኑ አዳዲስ አዳራሾች መከለላቸዉን ተመለከትኩ። የኦክሲጂን እጥረት አለ፣ የመድኃኒት እጥረት አለ፣ የባለሙያዎች ማነስ አለ!!
!!!

ወገኖቼ መጠንቀቁ ይበጀናል!!!

የጡት ካንሰር!!(ያወቅንዉን እናሳዉቅ!)የካንሰር በሽታ ከቅርብ ጊዚያት ወዲህ አለምን እየፈተኗት ከሚገኙ የጤና ተግዳሮቶች ዋንኛው ነው። የጡት ካንስር የበርካቶችን ህይወት እየቀጠፈ የሚገኝ በ...
16/01/2021

የጡት ካንሰር
!!
(ያወቅንዉን እናሳዉቅ!)
የካንሰር በሽታ ከቅርብ ጊዚያት ወዲህ አለምን እየፈተኗት ከሚገኙ የጤና ተግዳሮቶች ዋንኛው ነው። የጡት ካንስር የበርካቶችን ህይወት እየቀጠፈ የሚገኝ በሽታ ነው። በሴት እህቶቻችንና እናቶቻችን ከሚከሰቱ የካንሰር በሽታዎችም የመጀመሪያዉን ደረጃ ይይዛል፡ ዓለም አቀፍ ጥናቶች እንደሚያመለክቱትም ከሰምንት ሴቶች አንዷ በጡት ካንሰር ትጠቃለች፡፡ ሆኖም ለጤናችን ያለን ግንዛቤ ቢጨምር ይኽን ሞትን አፋጣኝ፡ ልጆችን ያለ እናት አስቀሪ በሽታ መግታትና መከላከል ይቻላል፡፡
* ስለ ጡት ካንሰር መረጃዎችን እንካችሁ ከማለቴ በፊት ስለ ካንሰር ትንሽ መረጃ ላጣቅሳችሁ ወደድኩ፡፡ በተፈጥሮ በሰውነታችን ውስጥ በብዙ ሚሊዮን የሚቆሩ ህዋሶች አሉ። እነዚህ ህዋሶች ይወለዳሉ፣ ያድጋሉ፣ ስራቸውን ከሰሩ በኋላም ይሞታሉ። አዳዲስ ህዋሳትም ሲፈጠሩም እንዲሞቱ ተደርገው ነው የሚሰሩት። አንዳንድ ጊዜ አስፈላጊ ሆኖ ሲገኝ እነዚህ ሴሎች ቁጥራቸው ይጨምራል። ለምሳሌ በኢንፌክሽን ጊዜ የነጭ ደም ሴሎች ቁጥር ይጨምራል፡፡ ካንሰር በሚፈጠር ጊዜ ግን ይህን የህዋሶች ሂደት ያስተጓጉለዋል። ካንሰር ሲይዝ ህዋሳት ስራቸውን ከጨረሱ በኋላ እንዳይሞቱ (immortal) ያደርጋቸዋል። አንዳንድ ጊዜ የደም አቅርቦት አጥሮ የሚመገቡት ሲያጡ ይሞቱ እንደሆነ ነው እንጂ ካንሰር ሲይዝ ህዋሳት በብዛት አይሞቱም። ቁጥራቸው በየጊዜው ባልተፈለገ መልኩ የሚቆጠር ይጨምራል። መጠናቸው እየጨመረ ሲመጣ አካባቢያቸው ያለውን የሰውነት ስራ ማወክ ይጀምራሉ፡፡....በሽታም ይሆናሉ፡፡
**ለጡት ካንሰር ተጋላጭነት እንደ ምክንየት የሚወሰዱትን ስንመለከት
1. ፆታ፡- የጡት ካንሰር 99% በመቶዉ በሴቶች የሚከሰት ቢሆንም ወንዶችም የችግሩ ሰለባ ተጠቂዎች ናቸዉ፡፡ ይኽንም ስናጤነዉ ሴቶች 100 እጥፍ ከወንዶች የበለጠ ለጡት ካንሰር ተጋላጭ ናቸዉ፡፡
2. እድሜ :- የጡት ካንሰር አብዛኛዉን ጊዜ እድሜያቸዉ ከ35-75 ዓመት ባሉ ሴቶች የሚከሰት ሲሆን በሀገራችን በ20ዎቹ የዕድሜ ክልል መመልከት የተለመደ ነዉ፡፡
3. የዘረ መል ችግርና በቤተሰብ መሸጋገር
BRCA 1 and BRCA 2 በዘረ መል 17 መገኘታቸዉ ተጋላጭነቱን ይጨምረዋል፡፡
4. የወር አበባ አመጣጥና አካሄድ:-
ከዕድሜ የፈጠነ የወረ አበባ ዑደት መጀመርና እና የማረጥ ጊዜ መዘግዬት
5. የደረት ለጨረር መጋለጥ፡- ወጣቶች ለ 'Hodgkin's Disease' የደረት የጨረር ህክምና ካገኙ በ50 አመታቸዉ በጡት ካንሰር የመጠቃት ዕድላቸዉ በ19% ይጨምራል፡፡
6. ጂኦግራፊዊ፡- የጡት ካንሰር በአብዛኛዉ የነጮች፡ የምዕራብዊያን በሽታ ተደረጎ ቢታይም አፍሪቃም የችግሩ ገፈት ቀማሽ ነች፡፡
7. ዉፍረትና የአልኮል መጠጥም እንደ ተጋላጭነትን ከሚጨምሩት ይጠቀሳሉ፡፡
የጡት ካንሰር ምልክቶችን ስንመለከት
1. በጡትና በጡት ዙሪያ እባጭ፡ ይኽ እባጭ ህመም የለሽና በድንገት ሊስተዋል ይችላል፡፡ ይኽ እባጭ በፍጥነት ሊያድግም ላያድግም ይችል ይሆናል፡፡ ይኽን ሲያስተዉሉ ወደ አቅራቢያ የጤና ተቋም መሄድ እንዳለበዎት ይገንዘቡ፡፡
2. የጡት መጠንና ቅርፅ መለያየት፡ የጡት ቆዳ ቀለም መለያየት..
3. የጡት ቆዳ መሰብሰብና የቆዳ መቆጣት፡ የቆዳ መጠንከርና መወጠር የመጀመሪያ ምልክት ሊሆኑ ይችላሉ፡፡
4. የጡት ጫፍ ወደ ውስጥ መገልበጥ ፡ መሰርጓድና የጡት ቆዳ ጥቃጥቆ ማዉጣት
5. የጡት ቁስል፡- የጡት ካንሰር አስፈላጊዉ ህክምና ካልተደረገለት ሊቆሳስልና ቁስሉ የመፈንዳት አጋጣሚ ሊኖረዉ ይችላል፡፡
5. የጡት ካንሰሩ በሰዉነት ከተሰራጨ በተለይም ወደ ሳንባ ከተዛመተ የትንፍሽ ማጠር፡ መድከም፡ ሳል መገለጫዎቹ ሊሆኑ ይችላሉ፡፡
6. አልፎ አልፎ በጡት አካባቢ የህመም ስሜት ሊኖርም ይችላል፡፡
እነዚህ ምልክቶች ያሉባቸዉ እህቶችና እናቶች ወደ ጤና ተቋም በመሄድ አስፈላጊዉን ምርመራ ማድረግ ይኖርባቸዋል፡፡ ምርመራዎች የጡት ካንሰር መሆኑን ካመላከቱ ደረጃዉ ይለያል፡፡ ደረጃ1 እና ደረጃ 2 የጡት ካንሰርን በቀዶ ጥገና ህክምና መታከም ይቻላል፡፡ ከ90% በላይ ህክምናዉ ስኬታማ ነዉ፡፡ በሰዉነት የተሰራጨ ከሆነ በጨረር ህክምናም ይታገዛል፡፡
'ታም ከመሟቀቅ አስቀድም መጠንቀቅ' እንዲሉ መከላከል ላይ ማመዘን ይገባናል፡፡ ለዚህ ደግሞ የጡት ካንሰር ከመከሰቱ አስቀድሞ ቅድመ ምርመራ-Screening ለማድረግ ሶስት አማራጮች አሉ፡፡
1ኛ.ሴቶች በየወሩ ጡታችሁን መፈተሽ ይኖርባችሁዋል-Breast Self Examination. ይኽም ጡታችሁን በደንብ፡ለማወቅና ልዩነቱን ለመገንዘብ ይረዳችሁዋል፡፡ የወረ አበባ የምታዩ ሴቶች በየወሩ የወረ አበባ ከጀመረበት ከ5 ቀን በሁዋላ ጡታችሁን ማስተዋል ይኖርባችሁዋል፡፡
2. ወደ ጤና ተቆም ብቅ በማለትም ምርመራ -Clinical Examination ማድረግ ይቻላል፡፡ ከ40 አመት በላይ የሆናችሁ ሴቶች በየአመቱ፡ ከ20-40 አመት ያላችሁ ሴቶች ደግሞ ቢያንስ በየ ሶስት አመቱ በጤና ባለሙያ መታየት ይኖርባቸዋል፡፡
3. የጡት ራጅ-Mammography
ከ40 ዓመት በላይ የሆናቸውና ምንም ምልክት የሌላችሁ ሴቶች በየአመቱ የጡት ራጅ ቢያሰሩ መልካም ነዉ፡፡
*የጡት ካንሰር በሀገራችን የብዙ እንስት ወገኖቻችን ህይወት እየቀጠፈ ይገኛልና ስለ በሽታዉ ያለንን ግንዛቤ በማስፋት አዉቀን አሳዉቀን የድርሻችንን እንወጣ፡፡

Address

Addis Abeba

Alerts

Be the first to know and let us send you an email when Dr.Gashaw Arega -ዶ/ር ጋሻዉ አረጋ posts news and promotions. Your email address will not be used for any other purpose, and you can unsubscribe at any time.

Contact The Practice

Send a message to Dr.Gashaw Arega -ዶ/ር ጋሻዉ አረጋ:

Share

Share on Facebook Share on Twitter Share on LinkedIn
Share on Pinterest Share on Reddit Share via Email
Share on WhatsApp Share on Instagram Share on Telegram