24/12/2021
በአማራ ክልል በአሸባሪው ህወሓት ወረራ ችግር ላይ ለወደቁ ከ11.4 ሚሊዮን በላይ ሰዎች አስቸኳይ ድጋፍ ያስፈልጋል
******************************
በአማራ ክልል በአሸባሪው ህወሓት ወረራ ምክንያት ችግር ላይ ለወደቁ 11 ነጥብ 4 ሚሊዮን በላይ ህዝብ አስቸኳይ ድጋፍ እንደሚያስፈልጋቸው የክልሉ የአደጋ መከላከልና ምግብ ዋስትና ኮሚሽን አስታወቀ።
አሸባሪ ቡድኑ በወረራ ይዟቸው በነበሩ አካባቢዎች ባለፋት 5 ወራት ምንም አይነት ድጋፍ ባለመደረጉ ዜጎች ለከፋ ችግር መጋለጣቸውንም ኮሚሽኑ አስታውቋል።
የአማራ ክልል አደጋ መከላከልና ምግብ ዋስትና ኮሚሽን ኮሚሽነር ዘላለም ልጃለም ጉዳዩን አስመልክተው ለጋዜጠኞች መግለጫ ሰጥተዋል።
አሸባሪው ህወሓት በፈፀመው ወረራ ከ2 ነጥብ 3 ሚሊዮን በላይ የሚሆኑ ከቀያቸው መፈናቀላቸውን እና 9 ሚሊዮን በላይ የሚሆኑ በአሸባሪ ቡድኑ በወረራ ተይዘው በቆዩ አካባቢዎች የሚኖሩ ዜጎች ለከፋ ችግር መዳረጋቸውን ኮሚሽነሩ ገልፀዋል።
በወረራው ምክንያት ለተፈናቀሉ ዜጎች ሰብአዊ ድግፋ ለማድረስ በመንግስት ፣ በተቋማት፣ በተራድዖ ድርጅቶችና በህብረተሰቡ ርብርብ ሲደረግ ቆይቷል ያሉት ኮሚሽነሩ አሁን ላይ በወረራ ተይዘው የነበሩ አካባቢወች ነፃ በመውጣታቸው ተፈናቃዮችን ወደቀያቸው የመመለስ ተግባር እየተከናወነ መሆኑንም ገልፀዋል።
እስካሁንም ከ160 ሺ በላይ ተፈናቃዮችን መመለስ ተችሏል ብለዋል።
አሸባሪው የህወሓት ሀይል በወረራ ይዟቸው በነበሩ አካባቢዎች ያደረሰው ሰብአዊና ቁሳዊ ጥፍት ከፍተኛ በመሆኑ ዜጎችን መልሶ ለማቋቋም በሚደረገው ጥረት ሁሉም አካል የበኩሉን አስተዋፅኦ እንዲያደርግም ኮሚሽነሩ ጥሪ አቅርበዋል።
አሁን ላይ በአሸባሪና ወራሪ ቡድኑ ምክንያት ችግር ላይ የወደቁ ዜጎችን ለመደገፍ በወር 1 ነጥብ 2 ሚሊዮን ኩንታል የእለት ደራሽ ምግብ እንደሚያስፈልግም ተናግረዋል።
15/4/14