31/07/2025
በዚህ ውድ 'ችግር' ላይ ‘መነገድ "ሃጢአትም-ኢሰብዓዊነትም" ነው !
መላኩ ብርሃኑ
| ኢትዮጵያ ውስጥ ኦቲዝም "እጅግ በጣም ውድ" ነው፡፡ ኦቲዝም ወደአንድ ቤት ሲመጣ በወላጅ ላይ ከሚፈጥረው ስነልቦናዊ ጉዳትና ከማህበራዊ ጫና ባሻገር የልጁን/ልጅቷን ህይወት ወደተሻለ ደረጃ ለማሸጋገር የሚደረገው ትግል እልህ አስጨራሽና ከፍተኛ ወጪ የሚጠይቅ ነው፡፡ ለዚህ ነው አንዳንዶች “ኦቲዝም የደሃ አይደለም” የሚሉት፡፡
ከ' ኦቲዝም ነው አይደለም' ምርመራና ብያኔ እንጀምር !
አንድ ልጅ የሚታዩበት ልዩ ኹኔታዎች የኦቲዝም ወይም ከኦቲዝም ጋር ተመሳሳይ የሆኑ ሌሎች የዐዕምሮ እድገት መዛባት ጉዳዮች መሆንና አለመሆናቸውን ለመለየት በሃገር ውስጥ የህክምና ማዕከላት የሚደረገው ምርመራ ዋጋው በጣም ውድ ነው፡፡ ከ20 ሺህ ብር ሊበልጥ ይችላል፡፡
በተጨማሪ ሃገር ውስጥ የሌሉ እንደ yeast overgrowth , zinc, lead እና ሌሎችንም ምርመራዎች ለማድረግ የደምና የሽንት ናሙናን ውጪ ሃገር ድረስ መላክን ይጠይቃል፡፡ ጄኔቲክ ምርመራዎችም አሉ፡፡ አቅም ላላቸውና ማሰራት ለሚችሉ ሰዎች እስከ100 ሺህ ብር ድረስ የሚጠይቅ ምርመራ ሊታዘዝ ይችላል፡፡
ምግብስ ቢሆን ?
በሌላ በኩል ኦቲዝም ያላቸው ልጆች ብዙውን ጊዜ ከአንጀታቸው ጋር የተያያዘ የጤና ችግር አለባቸው ተብሎ ይታመናል፡፡ አንጀታቸው አስራጊ (Leaky) ነው፡፡ ብዙ ጥናቶች ‘አንጀትን ማከም ኦቲዝምን ማከም ነው’ የሚል ድምዳሜ ላይ ስለደረሱ ህክምናውን ከአመጋገብ ለውጥ ጋር አስተሳስረውታል፡፡
“አንጀት ትንሹ አንጎል ነው” ይባላል ፡፡ የዶክተር ናታሻ ካምፕቤል የምርምር ውጤት የሆነው GAPS (Gut and Psychology Syndrome) የአመጋገብ ስርዓት (Diet) ለኦቲዝም ልጆች ድርድር የሌለበትና ካሉበት ኹኔታ ለማውጣት የሚጠቅም የአመጋገብ እቅድ የያዘ ነው ተብሎ ይታመንበታል፡፡
ስለሆነም በአብዛኛው ለኦቲዝም ልጆች የሚዘጋጀው ምግብ ኬዚን እና ግሉቲን የሚባሉትን ንጥረነገሮች የያዙና ለኦቲዝም መበየኛዎች (Symptoms) መባባስ ምክንያት የሚሆኑ ንጥረነገሮች በአንጀት ቀዳዳዎች ሾልከው ወደ ልጆቹ የደም ስርዓት ውስጥ እንዳይቀላቀሉ፣ ከዚያም ወደአንጎል ሄደው ስርዓቱን እንዳያቃውሱ ከምግብ ዝርዝር ውስጥ ሙሉ ለሙሉ ማስወገድን ይጠይቃል፡፡
ስለዚህ ወተትና የወተት ውጤቶች፣ እንዲሁም ስንዴና ገብስ እንዲሁም ከአጃ የሚሰሩ ማናቸውም ምግቦች የተከለከሉ ናቸው፡፡ ስኳርና ጣፋጭ ነገር (ከተፈጥሮአዊ ጣፋጮች በቀር) በጭራሽ አይፈቀዱም፡፡
በዚህ ሳቢያ ለልጆቹ አማራጭ ምግብ ለማዘጋጀት በርከት ያሉና እነዚህን ሊተኩ የሚችሉ ምግቦችን ማዘጋጀት ይፈልጋል፡፡ በተጨማሪ ደግሞ ከኦሜጋ 3 እና ከቫይታሚን ዲ በተጨማሪ በቁጥር ብዛት ያላቸው ምግብን የሚተኩ ንጥረነገሮችን (ፉድ ሰፕሊመንት) እንዲወስዱ ሊታዘዝ ይችላል፡፡ የእነዚያ ሰፕሊመንቶች ዋጋ ውድ ከመሆኑ ባሻገር ሁሉን ልተው ቢባል ቢያንስ የአንዱ ዋጋ ብቻ በወር እስከ 4 ሺህ ብር ወጪ ሊጠይቅ ይችላል፡፡ ቋሚ ነው፡፡ ይህንን በ5 እና 6 ሰፕሊመንቶች አብዙት፡፡ በዚህ ሳቢያ ለአንድ ኦቲዝም ላለበት ልጅ የሚወጣው የምግብ ወጪ አነድ ቤት ውስጥ ለመላው ቤተሰብ ቀለብ ከሚወጣው ወጪ ሊበልጥ ሁሉ ይችላል፡፡
ትምህርትስ እንዴት ነው?
ኦቲዝም በሽታ ስላልሆነ መድሃኒት የለውም፡፡ ለኦቲዝም የሚደረገው ህክምና በአብዛኛው ቴራፒ ነው፡፡ የስነባህሪ፣ የቋንቋ፣ የንግግር፣ የተግባቦት፣ የማህበራዊ ክህሎት ወዘተ ቴራፒዎች ናቸው ኦቲዝም ያለባቸውን ልጆች ለመርዳት እንደዋና የድጋፍ መስጫ መንገዶች የሚያገለግሉት፡፡ ኦቲዝምን “ውድ’ ከሚያደርጉት ነገሮች አንዱ ይህ ነው፡፡
እያንዳንዱ ቴራፒ ለዚያውም በቀን ከአንድ ሰዓት ያልበለጠ ሆኖ በወር የሚያስከፍለው ገንዘብ ግን አንድ ልጅን ዓመት የሚያስተምር ገንዘብ ነው፡፡ እንዲያም ሆኖ ረጅም ዓመት የሚፈልግ በመሆኑ ልጁንም ቶሎ ከድጋፍ ማላቀቅ አያስችልም፣ ውጤቱም ቶሎ አይታይም፡፡ ወላጆች ያለ የሌላቸውን ጥሪት ማውጣት ይጠበቅባቸዋል፡፡
በቁጥር ጥቂት የሆኑት 'የልዩ ፍላጎት አካቶ' ያላቸው ትምህርት ቤቶችም ቢሆኑ በወር ለአንድ ኦቲዝም ላለበት ልጅ የሚያስከፍሉት ገንዘብ ከመካከለኛው ዜጋ ኪስ በላይ ነው፡፡ አንዳንዱ ለማመንም፣ ለመጥራትም ይከብዳል፡፡ ኢንተርናሽናል ትምህርት ቤቶች እንኳን የማያስከፍሉትን አይነት ገንዘብ የሚያስከፍሉ አካቶ ት/ቤቶችና በኦቲዝም ስም የተቋቋሙ ተቋማት ብዙ ናቸው፡፡
በዚህ ላይ ልጁ ትምህርት ቤት ሲሄድም ሆነ ሲመለስ ሰርቪስ የሚጠቀም ከሆነ ወላጆች ለመጓጓዣው ከመደበኞቹ ህጻናት በእጥፍ እንዲከፍሉ ይደረጋል፡፡ በትከሻቸው ይሸከሙት ይመስል፡፡ በጣም ይገርመኛል መቼም፡፡ ኢትዮጵያ ውስጥ ያለው ልዩነትና አድልዎ በጣም ይሰቀጥጣል፡፡
በዚህ ሳያበቃ 'አካቶ' ብለው የሚቀበሉና ልዩ ዋጋ የሚያስከፍሉት ትምህርት ቤቶችም ቢሆኑ ሊያስተምሩ ከተቀበሏቸውና ኦቲዝም ካለባቸው ልጆች ጋር ትምህርት ቤት አብረው የሚውሉ 'አጋዦችን ( Assistant) እንዲቀጥሩ ወላጆችን ያስገድዳሉ፡፡ አንድ አጋዠ በወር 15 ሺህ ብር ድረስ ሊጠይቅ/ልትጠይቅ ትችላለች፡፡
ምንም ማለባበስ ሳያስፈልግ ኦቲዝም ኢትዮጵያ ውስጥ ላለ ወላጅ እንዲህ ተብሎ የማይገለጽ፣ ሌላው ሌላው ጫና ቀርቶ ከወጪ አንጻር ብቻ ህይወትን በጣም የሚያከብድ ውድ ነገር ነው፡፡ 'ለጊዜው አይወራ' ብለን የምንተወው ሌላ ብዙ ጫናም አለው፡፡ እነግዲህ በኢኮኖሚ በደደቀች ሃገር ለሚገኝ አንድ ለመኖርና ቤተሰቡን ለማኖር በሚንገታገት ወላጅ ላይ ኦቲዝም ሲደረብ ምን ያህል ከባድ ጫና መሆኑን ካሰባችሁት ይበቃል፡፡
እጅግ አስከፊው ነገር ግን ይህ ብቻ አይደለም !!
በዚህ 'ውድ' ችግር ላይ አይናቸውን አጥበው ገንዘብ የሚሰሩ ሰዎች መበርከታቸው ነው በጣም የሚያሳዝነው፡፡ አውቀው፣ ተምረው፣ ፍቃድ አግኝተው ልጆቹን መርዳት ችለው ቢሆን መልካም፡፡ ስለኦቲዝም ምንም ሳያውቁ ወይም ከኔ ባልተሻለ ጥቂት ንባብ ብቻ ተነስተው ቤት ተከራይተውና ማዕከል ከፍተው ‘ባለሙያ ነን’ ብለው ነው 'ቢዝነስ' የሚሰሩት ቲክቶኩንና ሶሻል ሚዲያውን አጣብበውታል፡፡
ያለሙያቸው 'ምርመራ' እናደርጋለን እያሉ 'ኦቲዝም ነው አይደለም' የሚለውን ከባድ ውጤት የሚበይኑ፣ እንችላለን ብለው የቋንቋና የባህሪ ህክምና ( ቴራፒ) ማዕከላት ከፍተው ብዙ ብር የሚቀበሉ ፣ "የንግግር ክህሎት፣ የባህሪ ማረቅ እና ቋንቋን መረዳት የሚያስተምሩ ፣ በአጠቃላይ የልዩ ፍላጎት ባለሙያዎችን እናሰለጥናለን" እያሉ የሚያስተዋውቁና የሚነግዱ 'ሳይማሩ አስተማሪ' ዎች በዝተዋል፡፡
ስለኦቲዝም ተገቢ ግንዛቤ የያዘ የመንግስት ተቋም በሌለባት፣ በቁጥር ከፍተኛ የሆነ'የኦቲዝም ማህበረሰብ' በምርጫ ማጣት ሳቢያ በግለሰብ አገልግሎት ሰጪዎች እጅ ላይ ብቻ በወደቀባት፣ በአጠቃላይ የኦቲዝም ስርጭትና ምጣኔ መረጃ (ዳታ) በሌላት ሃገር በተለይም በአዲስ አበባ ውስጥ 'ኦቲዝምን ቀላልና አትራፊ የንግድ ዘርፍ ' አድርገው ገንዘብ የሚሰበስቡ ሰዎች ቁጥር በጣም ተበራክቷል፡፡ በየዕለቱም ወደዚህ ዘርፍ 'አይንን በጨው አጥቦ' መግባት በርክቷል፡፡
ተስፋ አልባው ወላጅና አሳዛኞቹ ልጆች ደግሞ ባለማወቅ፣ አማራጭ በማጣትና በጭላንጭል ተስፋ ማስታወቂያ እየተከተሉ ከዚህ እዚያ 'ይሻላል' ብለው ይለፋሉ፡፡ ይህ ደግሞ ከገንዘቡም በላይ በወላጆችም ሆነ በልጆች ህይወትና የነገ ተስፋ ላይ ከባድና አደገኛ አደጋ ደቅኗል፡፡