Psych Addis - ሳይክ አዲስ

Psych Addis - ሳይክ አዲስ ይህ ገጽ የሥነ-ልቦና ሳይንስን ለሕይወታችን እንዲመች አድርገን እንድንጠቀም የሚያስችል መረጃ የምናገኝበት ነው:: ይከተሉንና አባል ይሁኑ!

ስለ እርግዝና ይህንን አዲስ ጥናት ልብ ይበሉ! የኮሎምቢያ ዩኒቨርሲቲ (Columbia University) ያካሄደው አስገራሚ ጥናት በእርግዝና ወቅት የሚፈጠር ከፍተኛ ጭንቀት በሚወለደው ሕፃን ...
29/12/2025

ስለ እርግዝና ይህንን አዲስ ጥናት ልብ ይበሉ!

የኮሎምቢያ ዩኒቨርሲቲ (Columbia University) ያካሄደው አስገራሚ ጥናት በእርግዝና ወቅት የሚፈጠር ከፍተኛ ጭንቀት በሚወለደው ሕፃን ጾታ ላይ ተጽእኖ እንዳለው አረጋግጧል።

ጥናቱ ምን አዲስ ነገር አገኘ?

▫️ወንዶች ለጭንቀት ይበልጥ ተጋላጭ ናቸው፤

በጭንቀት የተሞላ እርግዝና ሲኖር፣ ወንድ ፅንሶች (Male fetuses) ባላቸው ስነ-ህይወታዊ ተፈጥሮ ምክንያት የመቋቋም አቅማቸው ዝቅተኛ ነው። በዚህም ምክንያት ከመወለዳቸው በፊት የመቋረጥ ዕድላቸው ሰፊ ነው።

▫️ሴቶች ጠንካራ ናቸው፤

በአንፃሩ ሴት ፅንሶች አስቸጋሪ ሁኔታዎችን እና የናትን ጭንቀት ተቋቁሞ የመትረፍ ዕድላቸው ከፍተኛ ነው።

በቁጥር ሲታይ፤

▫️ከፍተኛ አካላዊ ጭንቀት የነበረባቸው እናቶች ከወለዱት ውስጥ 31% ብቻ ወንዶች ሲሆኑ፣

▫️ጤናማና ሰላማዊ እርግዝና ያሳለፉ እናቶች ጋር ግን ይህ ቁጥር ወደ 56% ከፍ ይላል።

ይህ የሚያሳየው እናትየዋ በጭንቀት ውስጥ በምትሆንበት ጊዜ ሴት ልጅ የመውለድ ዕድሏ እንደሚጨምር ነው። ሳይንቲስቶች ይህንን ሁኔታ፣ ተፈጥሮ ሴቶችን አስቸጋሪ ሁኔታዎችን እንዲቋቋሙ አድርጋ የፈጠረችበት መንገድ (Evolutionary response) እንደሆነ ይገምታሉ።

ጤናማ እና ደስተኛ እርግዝና እንዲሆንልዎ የህክምና ባለሙያዎች ምክር አይለይዎ! ❤️

መረጃው ለሌሎች እህቶች እንዲደርስ ሼር (Share) ያድርጉ! 🔄

ጠባሳው የት ነው ያለው? በስነ-ልቦና (Psychology) ታሪክ ውስጥ እጅግ አስደናቂ ከሆኑት ሙከራዎች አንዱ የሆነው "The Facial Scar Experiment" ይባላል። ውጤቱም ስለራሳች...
28/12/2025

ጠባሳው የት ነው ያለው?

በስነ-ልቦና (Psychology) ታሪክ ውስጥ እጅግ አስደናቂ ከሆኑት ሙከራዎች አንዱ የሆነው "The Facial Scar Experiment" ይባላል። ውጤቱም ስለራሳችን ያለንን አመለካከት እንድንፈትሽ ያደርገናል።

ሙከራው ምን ነበር?

ተመራማሪዎች በጎ ፈቃደኛ የሆኑ ሰዎችን ሰበሰቡና አንድ ሙከራ እንደሚሰሩ ነገሯቸው። ሙከራው "የፊት ላይ ጠባሳ ወይም የአካል ጉዳት ያለባቸው ሰዎች በህብረተሰቡ ውስጥ ምን አይነት አድልዎ ይደርስባቸዋል?" የሚለውን ለማጥናት ነበር።

እናም ሜካፕ አርቲስቶች ተጠሩና በእያንዳንዱ ተሳታፊ ፊት ላይ አስፈሪና ጎልቶ የሚታይ "የውሸት ጠባሳ" (Fake Scar) ሰሩላቸው። ተሳታፊዎቹም መስታወት ላይ ራሳቸውን አይተው ጠባሳው ምን ያህል ጎልቶ እንደሚታይ አረጋገጡ።

ጨዋታው እዚህ ጋር ነው!

ተሳታፊዎቹ ወደ ውጭ ወጥተው ከሰዎች ጋር ከመቀላቀላቸው በፊት፣ ሜካፕ አርቲስቷ የመጨረሻ ማስተካከያ እንደምታደርግና ጠባሳው እንዳይደርቅ ክሬም እንደምትቀባ ነገረቻቸው። ነገር ግን፣ ክሬም እየቀባች በማስመሰል ጠባሳውን ከፊታቸው ላይ አጠፋችው።

ተሳታፊዎቹ ግን ይህንን አያውቁም። ጠባሳው አሁንም ፊታቸው ላይ እንዳለ አድርገው በማሰብ፣ እያንዳንዳቸው ወደ ተለያየ ቢሮ ሄደው ከማያውቋቸው ሰዎች ጋር ተገናኙ።

ውጤቱ ምን ነበር?

ተሳታፊዎቹ ተመልሰው ሲመጡ ሪፖርት ያደረጉት ነገር አስገራሚ ነበር። ሁሉም ማለት ይቻላል እንዲህ አሉ፡-

▫️"ሰዎች በሩቅ ሲሸሹኝ ነበር።"

▫️"እያፈጠጡብኝ ተቸገርኩ።"

▫️"ንግግራቸው እና አመለካከታቸው የመጸየፍ ነበር።"

አንዳንዶቹማ "እንዲህ አይነት ቃል ተናገሩኝ" ብለው በዝርዝር አስረዱ። ነገር ግን እውነታው ፊታቸው ላይ ምንም ጠባሳ አልነበረም! ሰዎች ያዩዋቸው እንደ ማንኛውም ጤናማ ሰው ነበር።

ከዚህ ምን እንማራለን?

▫️ እምነት/እይታ እውነታን ይፈጥራል፣

ሰዎች ለእኛ የሚሰጡን ምላሽ የሚወሰነው፤ እኛ ስለራሳችን ባለን ስሜት ነው። እኛ በራሳችን ላይ የጎደለ ነገር አለ ብለን ካሰብን፣ የሰዎችን እይታና ንግግር በዚያው ልክ ተርጉመን እንረዳዋለን።

▫️ የአእምሮ "ጠባሳ"፣

ብዙ ጊዜ በራስ መተማመን የሚያሳጣን አካላዊ ቁመናችን ሳይሆን፤ አእምሯችን ውስጥ የሳልነው የራሳችን ምስል ነው።

▫️ ራስን መቀበል፣

አንተ ራስህን ስትቀበል፣ አለምም ይቀበልሃል። ጉድለት አለብኝ ብለህ ስታስብ ግን፣ በሰዎች ንግግር ውስጥ ጉድለትህን የሚነካ ነገር ስትፈልግ ትውላለህ።

እናም ይህንን ተረዱ፣

ዛሬ ወደ ውጭ ስትወጡ፤ ፊታችሁ ላይ ሳይሆን አእምሯችሁ ላይ ያለውን "ጠባሳ" አጥፉት።
▫️ቀና ብላችሁ ተራመዱ፣
▫️ፈግግ በሉ፣
▫️በራሳችሁ ተማመኑ።

አለም የምታየው እናንተ የምታሳዩዋትን ነው።

ይህን መልእክት ለሌሎች እንዲደርስ Like እና Share ያድርጉ! ❤️

ሕይወትህን በድብቅ የሚዘውረው ማነው? ብዙዎቻችን በሥራችን፣ በገንዘብ አያያዛችን ወይም በግንኙነታችን ስኬታማ ለመሆን እንጥራለን። ነገር ግን ምንም ያህል ብንሮጥ፣ አንድ የማይታይ ገመድ ወደ ...
28/12/2025

ሕይወትህን በድብቅ የሚዘውረው ማነው?

ብዙዎቻችን በሥራችን፣ በገንዘብ አያያዛችን ወይም በግንኙነታችን ስኬታማ ለመሆን እንጥራለን። ነገር ግን ምንም ያህል ብንሮጥ፣ አንድ የማይታይ ገመድ ወደ ኋላ የሚጎትተን ይመስለናል።

ምክንያቱስ?

በልጅነታችን ያልታየው፣ ያልታቀፈው እና ስሜቱ ያልተደመጠለት ያ የውስጥ ማንነታችን (Wounded Inner Child)፣ ዛሬ ላይ ከመጋረጃ በስተጀርባ ሆኖ ሕይወታችንን ይዘውረዋል።

ይህ ጉዳይ በድብቁ አዕምሯችን (Subconscious) ጥልቀት ውስጥ ብቻ ሳይሆን፣ በነርቭ ስርዓታችን (Nervous System) ውስጥም ታትሞ የተቀመጠ ነው። ይህንን እውነት መካድ ከባድ ነው።

⚠️ ይህንን የልጅነት ቁስል፡-
🚫 በሎጂክ ወይም በእውቀት ልንረታው፣
🚫 በመንፈሳዊነት ልንዘለው (አንዳንዴ ካልሆነ በስተቀር)፣
🚫 ወይም በሱሶች ልንሸፍነው አንችልም።

ሰውነታችን የሚፈልገው አንድ ነገር ነው፤ እሱም እንድንረጋጋ (Slow down)፣ ህመሙን እንድናየው እና ማንም ባላሳየን መንገድ ለራሳችን እውቅና በመስጠት፣ ሰውነታችን ያንን ስሜት እንዲያስተናግደው መፍቀድ ነው።

እውነተኛ ስኬት የሚጀምረው ከውጭ ሳይሆን፣ ይህንን የውስጥ ሰላም ከመፍጠር ነው።

እናንተስ ተመሳሳይ ስሜት ተሰምቷችሁ ያውቃል?

የማህበራዊ ሥነ-ልቦና ሳይንስ አንድ ሰው በሌሎች መኖር ምክንያት የሚደርስበትን ተጽዕኖ ወይም የእርሱ መኖር በሌሎች ላይ የሚያደርገውን ተጽዕኖ የሚያጠና ሳይንስ ነው፡፡ ይህም ማለት በማህበራዊ...
27/12/2025

የማህበራዊ ሥነ-ልቦና ሳይንስ አንድ ሰው በሌሎች መኖር ምክንያት የሚደርስበትን ተጽዕኖ ወይም የእርሱ መኖር በሌሎች ላይ የሚያደርገውን ተጽዕኖ የሚያጠና ሳይንስ ነው፡፡ ይህም ማለት በማህበራዊ መስተጋብር በሚፈጠር ግንኙነት የተነሳ አንዱ ሌላው ላይ ወይም ሌላው አንዱ ላይ የሚያሳድሩትን ተጽዕኖ ያጠቃልላል፡፡ በዚህም ሌሎች ሰዎችን የምናይበት መንገድ በዚህ ተጽዕኖ ምክንያት የተለያየ ይሆናል ማለት ነው፡፡

ይህንን ተከትሎም ማህበራዊ ግንኙነታችን ሁልጊዜ የተዋጣለት ላይሆን ይችላል። አንዳንዶች ጋር መልካምና ዘላቂ የሆነ ግንኙነት መፍጠር ስንችል ከሌሎች ጋር ደግሞ በተቃራኒው ሊሆን ይችላል። በዚህም ከማን ጋር መልካም ግንኙነት መፍጠር እንዳለብንና እንደሌለብን መጠንቀቅ ይኖርብናል። ከሚዋሹን፣ ለእኛ ክብር ከሌላቸው፣ መጠቀሚያ ከሚያደርጉን፣ ዝቅ አድርገው ከሚመለከቱንና ወደ ኋላ ከሚጎትቱን ሰዎች መራቅ ያስፈልጋል። ምክንያቱም እንዲህ አይነት ሰዎች ዋጋችንን የሚያሳንሱ ናቸውና ቢቀሩብን እንጠቀማለን እንጅ አንዳችም ጉዳት አይደርስብንም።

ይህን ሊንክ በመጫን SUBSCRIBE ማድረግዎን ያረጋግጡ!
YouTube: 👉https://www.youtube.com/channel/UCnCr33gnQ5WY-gvWz4Ef5Fw?sub_confirmation=1
Telegram: 👉t.me/psychaddis

የትምህርት ተቋማት የተማሪዎችን ሕይወት በመቅረጽ፣ ባህርያቸውን በማስተካከል፣ ሥነ-ሥርዓት በማስተማር ከቤተሰብ ቀጥሎ ትልቁን ድርሻ ይይዛሉ። እነዚህ ተቋማት ከኬጂ ጀምሮ እስከ ኮሌጅና ዩኒቨር...
27/12/2025

የትምህርት ተቋማት የተማሪዎችን ሕይወት በመቅረጽ፣ ባህርያቸውን በማስተካከል፣ ሥነ-ሥርዓት በማስተማር ከቤተሰብ ቀጥሎ ትልቁን ድርሻ ይይዛሉ። እነዚህ ተቋማት ከኬጂ ጀምሮ እስከ ኮሌጅና ዩኒቨርሲቲዎች ድረስ ተማሪዎችን በማብቃት ረገድ ከፍተኛ ሚና ይጫዎታሉ።

በትምህርት ቤት፣ ኮሌጅና ዩኒቨርሲቲ የሚያስተምሩ መምህራን የተማሪዎቻቸውን የወደፊት ሕይወት በማስተካከል፣ የአርአያነት ሚናቸውን በመወጣት መልካም ምግባር የተላበሰን ዜጋ በማፍራት ከፍተኛ ሥራ ይሰራሉ። ለዚህም ምስጋና ይገባቸዋል።

በአንጻሩ ደግሞ በተለይም ወደ ሀገራችን ስንመጣ ከቤተሰብ ጀምሮ በልጆች የባህርይ ቀረጻ ላይ እየተሰሩ ያሉ ሥራዎች በጣም አነስተኛ ከመሆናቸውም ባሻገር በተለይም አንዳንድ መምህራን የተማሪዎችን ስብዕና በማውረድ፣ የማይረቡና ምንም ዋጋ የሌላቸው መሆኑን በመናገር፣ እንዲሁም በመፈረጅ የሚያሸማቅቁበትና የልጆችን ሞራል የሚነኩበት ድርጊት እጅግ አሳዛኝና አስደንጋጭ ነው።

በመሰረቱ እንዲህ የሚያደርጉ ሰዎች ጥቂት ቢሆኑም የሚያደርሱት ጉዳት ግን እጅግ ውስብስብና በተለይም ተማሪዎችን ወደ አላስፈላጊ ችግር ውስጥ የሚከት ስለሆነ ይህ ድርጊት መወገድ ይኖርበታል። ይህንን ስንል ከሰዎች ሥነ-ልቦናዊ ስሪትና ስብዕና ግንባታ አንጻር ብቻም ሳይሆን የወደፊት አጥፊዎችን ጭምር በመቀነስ ደረጃ ከፍተኛ አስተዋጽኦ ከማድረጉም ባሻገር ጤነኛና አምራች ዜጋን በመገንባት ረገድ ከፍተኛ ድርሻ ስላለው ነው። ምክንያቱም በልጅነት አዕምሮ የተገነባን ነገር ለማፍረስ እጅግ ብዙ ዋጋና ጊዜ ይጠይቃልና ነው።

ይህንን ድርጊት ለማስቆምም ሆነ ለመቀነስ በየተቋማቱ ያሉ የሥነ-ልቦና ባለሙያዎችና መልካም ምግባር የተላበሱ መምህራን ከፍተኛውን ድርሻ ሊወጡ ይገባል። በተለይም የሥነ-ልቦና ባለሙያዎች ለመምህራን የክፍል አያያዝና አስተዳደር ሥልጠና በመስጠት፣ የተማሪዎች አያያዝና ሥነ-ምግባር ግንባታ ላይ ሥልጠና በመስጠት፣ ተማሪዎችንም ሆነ መምህራንን ስለ ራስን መግዛትና ንዴትን መቆጣጠር ላይ ያተኮሩ ሥልጠናዎችን በመስጠት እንዲሁም ተማሪዎችን ለይቶ ለሚያሳዩት ባህርይ ቅጣትና ሽልማት በመስጠት መልካም ምግባር እንዲያጎለብቱ ማገዝ ይገባል። የሚመለከታቸው ኃላፊዎችም ይህንን በማገዝ ዘመናዊ የሆነና በባለሙያ የታገዘ ሥነ-ምግባር ግንባታ የበኩላቸውን ሚና ሊወጡ ይገባል እንላለን።

እኛም ይህንን አሳሳቢ ጉዳይ ለመቀነስ ይቻል ዘንድ ሥልጠናዎቹን ለመስጠት በዝግጅት ላይ እንገኛለን። ሥልጠናውን ልምድ ባላቸው ባለሙያዎች እንዲሰጥላችሁ የምትፈልጉ የግልና የመንግስት የትምህርት ተቋማት፣ የትምህርት ቤት ኃላፊዎች፣ መምህራንና ሌሎች የሥራ ኃላፊዎች በውስጥ መስመር መልዕክት ላኩልን።

ይህን ሊንክ በመጫን SUBSCRIBE ማድረግዎን ያረጋግጡ!
👉https://www.youtube.com/channel/UCnCr33gnQ5WY-gvWz4Ef5Fw?sub_confirmation=1

🛑 ልጅ ከመውለድህ በፊት ራስህን ፈውስ! ▫️ከወለድክም ትራውማህን አታስተላልፍ!በየሶሻል ሚዲያው፣ በየታክሲውና በየአካባቢው ጩኸቱ ይሰማሃል? "ትዳር በረከት አጣ"፣ "ፍቺ በዛ"፣ "የዘንድሮ ...
22/12/2025

🛑 ልጅ ከመውለድህ በፊት ራስህን ፈውስ!
▫️ከወለድክም ትራውማህን አታስተላልፍ!

በየሶሻል ሚዲያው፣ በየታክሲውና በየአካባቢው ጩኸቱ ይሰማሃል?

"ትዳር በረከት አጣ"፣ "ፍቺ በዛ"፣ "የዘንድሮ ልጆች አይሰሙም/ባለጌ ሆኑ"፣ "ማህበረሰቡ ተበላሸ፣ ፍቅር ጠፋ..." የሚለው እሮሮ በዝቷል። እውነት ነው፤ ብዙ ነገሮች ተበላሽተዋል።

ነገር ግን የምንሰጠው ምክንያትና መፍትሄ ላይ ትልቅ ስህተት አለ።

ብዙዎቻችን "ልጅ ሲመጣ ትዳሩ ይስተካከላል" ወይም "ልጅ ለቤቱ ድምቀት ነው" በሚል የራሳችንን ባዶነት ለመሙላት ብቻ እንወልዳለን። እውነታው ግን የመጣው ልጅ የትዳር ማስተካከያ ወይም የብቸኝነት ማስታገሻ ኪኒን አይደለም።

በኢትዮጵያዊ የልጅ አስተዳደግ ልማዳችን ውስጥ ብዙ ያልተሰሩ የቤት ስራዎች አሉ። ዛሬ የምናየው "የማህበረሰብ መበላሸት" የድሮ "የአስተዳደግ ክፍተት" ውጤት ነው። ይህ ክፍተት በብዙ ምክንያቶች የመጣ ነው። (ምክንያቶቹን ሌላ ጊዜ እንመለስባቸዋለን።)

ለምን?
ጥናቶችስ ምን ይላሉ?

ይህ የምናወራው ጉዳይ ከባዶ ሜዳ የተነሳ ስሜት አይደለም። በዓለም አቀፍ ደረጃ የተደረጉ ግዙፍ ሳይንሳዊ ጥናቶች (Meta-Analyses on Adverse Childhood Experiences - ACEs) የሚያረጋግጡት አስደንጋጭ እውነታ አለ።

በተለያዩ ሀገራት የተደረጉ በርካታ ጥናቶችን ያጠቃለለ ሜታ-አናሊሲስ እንደሚያሳየው፤ በልጅነታቸው የስነ-ልቦና ቁስል፣ የአካል መቁሰል፣ ወይም የቤተሰብ ፍቅር ማጣት (Neglect) ያጋጠማቸው ልጆች፣ ወደ አዋቂነት ሲሸጋገሩ፡-

1. ለአዕምሮ ጤና ቀውስ (ድብርት፣ ጭንቀት፣ ራስን ማጥፋት) የመጋለጥ እድላቸው እጅግ ከፍተኛ ነው።

2. ለሱስ እና ለአደገኛ ባህሪያት ይጋለጣሉ (ይህ ዛሬ የምናየውን የወጣቶች "መበላሸት" የምንለውን ያጠቃልላል)።

3. ጤናማ ትዳር እና ማህበራዊ ግንኙነት መመስረት ይቸገራሉ። ምክንያቱም ያላገኙትን ፍቅርና መተማመን መስጠት አይችሉም።

ስለዚህም፣

1. ያልዳነ ቁስል (Trauma) ታቅፎ ልጅ መውለድ ምን ያስከትላል?

ብዙ ወላጆች ከልጅነታቸው የመጣ ያልዳነ የሥነ-ልቦና ቁስል (Trauma) አለባቸው። በልጅነትህ ተገፍተህ፣ ተረግጠህ ወይም ፍቅር ተነፍገህ ካደክና ይሄንን ሳታክም አንተም ልጅ ከወለድክ፤ ያንኑ ህመም ሳታውቀው ለልጅህ ታወርሳለህ። የምትጮኸው፣ የምትናደደው፣ ወይም ልጁን የምትቀጣው ልጁ ስላጠፋ ብቻ ሳይሆን ያንተ የውስጥ ህመም ስለተነካ ነው።

2. ዲሲፕሊን ወይስ የበቀል እርምጃ?

ልጆች ሲያጠፉ የምንወስደው እርምጃ ማረም ወይስ መቅጣት? በኢትዮጵያ ብዙ ቤተሰቦች ውስጥ "ዲሲፕሊን/ሥነሥርዓት" ማለት ማስፈራራት፣ መደብደብና ማሸማቀቅ ነው። ይህ ደግሞ ነገ እልህ የሚጋባ፣ ለራሱ ክብር የሌለው፣ በትንሽ ነገር ትዳሩን የሚያፈርስና ከሰው ጋር መኖር የማይችል "የቆሰለ ትውልድ" ይፈጥራል።

3. የትኩረት ማነስ (Emotional Neglect)፣

ልጆች ከምግብና ልብስ በላይ "መደመጥን" ይፈልጋሉ። እያንዳንዳቸው ዛሬ የምናማርርባቸው ወጣቶች ቢጠየቁ፤ በልጅነታቸው "አባቴ አይሰማኝም"፣ "እናቴ አትረዳኝም" ብለው ያደጉ ናቸው። ቤቱ ውስጥ ያጣውን ፍቅርና ትኩረት ፍለጋ ወደ ውጭ ሲወጣ ነው ማህበረሰቡ "ተበላሸ/ ስድ ሆነ" የሚለው። ልጅ ሲበላሽ ተጠያቂው አካባቢው ወይም ሰፈሩ ብቻ ሳይሆን፤ የልጁን ስሜት ያላደመጠው ቤተሰብም ጭምር ነው።

ወዳጄ!

ልጅ መውለድ ቀላል ነው፤ "ሰው መፍጠር" ግን ከባድ ነው። ያልዳነ ሰው ሌላ የቆሰለ ሰው ይፈጥራል። ትዳር የሚፈርሰው፣ ማህበረሰቡ የሚታወከው እኮ ሰዎች በልጅነታቸው ያላገኙትን ፍቅርና ክብር በጉልበት ለማግኘት ሲሞክሩ ነው።

ስለዚህ ሰንሰለቱን እንበጥስ!

▫️ከመውለድህ በፊት ራስህን ፈትሽ።
▫️ያለፈ ህመምህን አክም።
▫️ልጅን "ንብረትህ" ሳይሆን "አደራህ" አድርገህ ተቀበል።
▫️ጊዜ ስጠው፣ አድምጠው፣ ቅረበው።

የተሻለች ሀገር፣ የሰከነ ትዳርና መልካም ትውልድ የሚገኘው ዛሬ በምንወልደው ልጅ ላይ በምንሰራው የሥነ-ልቦና ፈውስ ነው።

ለልጅህ የምታወርሰው ምርጥ ቅርስ "የዳነና ጤናማ አዕምሮ ያለው ወላጅ" መሆንህን ነው።

ይህ መልእክት ለሌሎች እንዲደርስ ሼር በማድረግ የድርሻዎን ይወጡ!

ማሳሰቢያ⁉️
ይህ በጥናት ላይ የተመሰረተ እና በየትኛውም አገር ላይ የሚሰራ ነው። ያደጉ አገራትም ከትራውማ ነጻ አለመሆናቸውን እና ጥናቱ በእነሱ ላይ እንደተሰራም ጭምር ልብ ማለት ያስፈልጋል። በአሜሪካ እንኳን 64% የሚሆኑት አዋቂ ሰዎች ከ18 ዓመታቸው በፊት ቢያንስ አንድ ጊዜ አጋጥሟቸው ያውቃል። ከ6 ሰዎች አንዱ ደግሞ 4 እና ከዚያ በላይ ትራውማዎች ደርሰውበታል።

21/12/2025

ሴቶች ወንዶች ሲያደርጉት የሚጠሉት ባህርይ፣ ነገር ግን በውስጣቸው እንዲያደርጉት የሚፈልጉት ነገር አለ?
👇👇👇
የመጀመሪያ ኮሜንት ላይ ተመልከቱ!

21/12/2025

በልጅነታችሁ በወላጆቻችሁ ያለጥፋታችሁ ተደብድባችሁ ነገር ግን ጥፋቱ የሌላ ሰው እንደሆነ ከታወቀ በኋላ ይቅርታ ተጠይቃችሁ ታውቃላችሁ?
👇👇👇
ኮመንት ጻፉ፣ ሀሳባችሁን አካፍሉን!

አንዳንድ ሰዎች በእኛ ሕይወት፣ ሥራ፣ ሀሳብ፣ ፍልስፍናና የአኗኗር ዘይቤ ገብተው ሲበጠብጡን፣ ነገሮችን ሲያወሳስቡብን፣ አልፎ ተርፎም ከባድ ተጽዕኖ ውስጥ ሲከቱን እናያለን። ይህን ጊዜ የእኛን...
20/12/2025

አንዳንድ ሰዎች በእኛ ሕይወት፣ ሥራ፣ ሀሳብ፣ ፍልስፍናና የአኗኗር ዘይቤ ገብተው ሲበጠብጡን፣ ነገሮችን ሲያወሳስቡብን፣ አልፎ ተርፎም ከባድ ተጽዕኖ ውስጥ ሲከቱን እናያለን።

ይህን ጊዜ የእኛን ማንነት የምናሳይበት፣ ወሰናችንን ጥሰው የገቡትን ልክ የምናስገባበት፣ ትክክለኛ ቦታቸው የት እንደሆነ የምንነግርበትና አደብ የምናስገዛበት ትክክለኛ ወቅት ይመጣል። ልክ ታላቁ ማሀተማ ጋንዲ " ማንም በቆሸሸ እግሩ በአዕምሮዬ እንዲመላለስ አልፈቅድለትም" እንዳለው።

እንዲህ አይነት ሁኔታ ሲገጥመን ግን የእኛን ስብዕና በማይነካና በቀጣይ ወደ ሌላ መጥፎ ሁኔታ ውስጥ በሚከተን አኳኋን መሆን የለበትም።

ሰብስክራይብ ያድርጉና ቤተሰብ ይሁኑ!

ለዩቲዩብ: እዚህ ይጫኑ👉https://youtu.be/PDUCC1WD5mw
ለቴሌግራም: እዚህ ይጫኑ👉 https://t.me/psychaddis

ወዳጄ ሆይ!(Reposted After 4 Years)ሁሉን ነገር አትመን፣ ሁሉንም ነገር አትጠራጠር። ብቻ የላቀ የንቃተ-ህሊና ባለቤት ሁን። ይህ ማለት ስለ አካባቢህ እወቅ፣ ዙሪያህን ተረዳ፣ ራ...
19/12/2025

ወዳጄ ሆይ!
(Reposted After 4 Years)

ሁሉን ነገር አትመን፣ ሁሉንም ነገር አትጠራጠር። ብቻ የላቀ የንቃተ-ህሊና ባለቤት ሁን። ይህ ማለት ስለ አካባቢህ እወቅ፣ ዙሪያህን ተረዳ፣ ራስህን እወቅ፣ የምትችለውንና የማትችለውን ለይ። ስለማታውቀው ነገር ለማወቅ ጣር እንጂ አትዘባርቅ። የምታየው ሁሉ እውነት አይደለም፣ የሰማኸው ሁሉ የሚታመን አይደለም። እናም ወዳጄ ረጋ በል፣ ሁሉን አውቃለሁ አትበል፣ ለሚያውቁ ቅድሚያ ስጥ። ስላልገባህ ጉዳይ ጠይቅ፣ ለማወቅ ጉጉት ይኑርህ። በሰው ጉዳይ ጥልቅ አትበል፣ የራስህን ሕይወት ውብ አድርገህ ኑር።

ማንም ከተኛህበት አያነቃህም፣ ማንም ከወደቅህበት አያነሳህም። ማንም የአንተን ሕይወት አይኖርም፣ ማንም የአንተን ሞት አይሞትም። ወደዚህ ምድር ስትመጣ ብቻህን እንደሆነ ሁሉ ከዚህ ምድር ስትሄድም ብቻህን ነህ። እናም ለማንም ብለህ ሕልምህን አታጨናግፍ፣ ለምንም ብለህ በሰው አስተያዬት አትሸማቀቅ። አንተ እኮ ወደዚህ ስትላክ የተሰጠህ ተልዕኮ አለ፣ ውስጥህ እያቃጨለ የሚኖር፣ ልውጣ አልውጣ እያለ የሚታገል ኃያል መክሊት አለ። አዳምጠው፣ ፈልገው፣ አግኘው፣ አውጣው። የተመቻቸ ጊዜና ቦታ ስትፈልግ መልሰህ ይዘኸው መሄድ ይሻልሃል ወይስ በእያንዳንዷ ቀን እየኖርከው አሻራህን ጥለህ ማለፍ? ምርጫው የአንተ ብቻ ነው።

ወዳጄ ልጅ ስለወለድክ ታሪክህ አይተላለፍም፣ ወይም ስምህ አይነሳም። የተለየና የራስህ የሆነ ደማቅ ታሪክ ስለሰራህ እንጅ። ብዙ ሰው ማግባትና መውለድን ትልቅ የሕይወት ግቡ አድርጎ ይኖራል፣ ነገር ግን ካገባና ከወለደም በኋላ የሚፈልገውን ሕይወት ሳይኖር ያልፋል። ለምን ይመስልሃል? መጀመሪያውኑም የሕይወት ግብ ምን እንደሆነ ስለማያውቅ ነው። ብታገባና ቤተሰብ ብትመሰርት መልካም ነው፣ ነገር ግን ምን አይነት ቤተሰብ እንደሚኖርህ ካላሰብክ፣ ምን አይነት ልጅ እንደምታሳድግ ካላቀድክ ከስረሃል፣ ሕይወትን አልኖርክም። የአንተንም ሆነ የሌላውን ልጅ፣ ጭራሽ ዘመኑንም ስትወቅስና ስታማርር መኖርህ ነው።

ወዳጄ ንቃ። ከራስህ ጋር ተወዳደር። አግባ፣ ውለድ፣ ቤት ግዛ፣ መኪና ግዛ፣ ወዘተ የሚሉህ ሰዎች ለአንተ መልካም አስበው ነውና ብዙም አትፍረድባቸው። ነገር ግን ዓላማህን የምታውቀው አንተ ብቻ ነህ። ከላይ የተጠቀሱት ነገሮች ባይኖሩህም የጸና አላማ ይኑርህ፣ እነዚህ በአንተ ፈቃድ ላይ የተመሰረቱ ናቸውና መቼም ቢሆን ታገኛቸዋለህ። እናም ራስህን ሆነህ ኑር። ለአላማህ መስዋዕትነት ክፈል። ያኔ ታሪክ ይኖርሃል። አዎ ካላሸነፍክ ለአንተ ታሪክ ማንም ግድ አይሰጠውም፣ ስለሆነም አሸንፍ!

በነገራችን ላይ ሰው ትዝታውን ነው የሚኖረው። ልጅነቱን፣ ወጣትነቱን፣ ያሳለፈውን። ለዚህም ነው ትዝታውን የሚያመሰግነው፣ ምንም እንኳን ያኔ ሲያደርገው አብዛኛውን ጊዜ እንዲህ ይሆናል ብሎ ባይገምትም። ለዚህ ነው የታሪክ (የትዝታ) መሥሪያ ብቸኛ ጊዜ አሁን ነው የምልህ። አሁን ላይ የሰራኸው ሁሉ አንተ እያለህ ትዝታህ፣ አንተ ስታልፍ ደግሞ ታሪክህ ይሆናልና።

ይህን ሊንክ በመጫን SUBSCRIBE ማድረግዎን ያረጋግጡ!
👉https://www.youtube.com/channel/UCnCr33gnQ5WY-gvWz4Ef5Fw?sub_confirmation=1

Address

AAU
Addis Ababa
1000

Alerts

Be the first to know and let us send you an email when Psych Addis - ሳይክ አዲስ posts news and promotions. Your email address will not be used for any other purpose, and you can unsubscribe at any time.

Contact The Practice

Send a message to Psych Addis - ሳይክ አዲስ:

Share

Share on Facebook Share on Twitter Share on LinkedIn
Share on Pinterest Share on Reddit Share via Email
Share on WhatsApp Share on Instagram Share on Telegram

Category