05/02/2026
ኩልና የአይን ጤና
ሺህ ዘመናት የተሻገረው ኩል ለጤና እና ለውበት ያለው ጥቅም
ዘመነኛው የመዋቢያ ምርት አቅራቢ ዓለም 'eyeliner' ይለዋል። ኩል በተለያየ መንገድ ገበያ ላይ ቢቀርብም ታሪኩ ዓመታትን ወደኋላ ይሻገራል።
ዘሐራ ሀንከር የቢቢሲ ጋዜጠኛ ናት። ብሩክሊን የሚገኘው ቤቷ ውስጥ ኩል ስትቀባ "ከቤቴ ብርቅም ከእናቴ፣ ከአያቴ እና ከመካከለኛው ምሥራቅ ሴቶች ጋር የተሳሰርኩ ይመስለኛል" ስትል ትገልጻለች።
ያለፈው ታኅሣሥ ላይ የተባበሩት መንግሥታት የትምህርት፣ ሳይንስ እና ባህል ተቋም በዓለም የማይዳሰሱ ቅርሶች ዝርዝር ውስጥ ኩልን አካቷል።
ሴቶችም ወንዶችም ዐይናቸው ላይ የሚያደርጉት ኩል ሺህ ዓመታት የተሻገረ ታሪክ አለው።
ኩል አረብኛ ቃል ነው። ከአረቡ ዓለም ባሻገር በኢትዮጵያ የሚጠራውም በዚህ ስሙ ቢሆንም በተለያዩ ባህሎች የተለያየ ስም አለው።
ደቡብ አፍሪካ ካጃል፣ ናይጄሪያ ትሪዮ፣ ኢራን ሶርማህ ይባላል።
ኩል በባህላዊ መንገድ ይዘጋጃል
Road mlpp@አንቲሞኒ እና ሊድ የተባሉት ንጥረ ነገሮች በዋናነት ጥቅም ላይ እንደሚውሉ ሊባኖሳዊ-እንግሊዛዊቷ ዘሐራ ሀንከር ትናገራለች።
በእርስ በርስ ጦርነቱ ምክንያት ከቤተሰቧ ጋር ወደ እንግሊዝ ሸሽተዋል።
"እናቴ መዋቢያ ስትጠቀም እመለከታት ነበር። ጥልቅ ከሆነ ነገር ጋር የምትተሳሰርበት መንገድ ነው ብዬ አምናለሁ" ትላለች።
ስለ ኩል 'Eyeliner: A Cultural History' የተባለ መጽሐፍ የጻፈችው ዘሐራ እንደምትለው ዩኔስኮ ኩልን ቅርስ አድርጎ መመዝገቡ "ኩል ጊዜያዊ ሳይሆን ጥበቃ የሚፈልግ ባህላዊ ክንውን መሆኑን" ያሳያል።
"እንዲህ ያለ ዕውቅና ማግኘቱ የኩል አሠራር እና አጠቃቀም ባህል ተጠብቆ እንዲቆይ ይረዳል። ተሰንዶ ከትውልድ ትውልድ እንዲሸጋገርም ያግዛል። በአንድ ትውልድ ተገድቦ የሚቆይ ወይም በዓለም መዋቢያ ምርቶች ንግድ ውስጥ የሚጠፋ አይሆንም" ስትል ታስረዳለች።
ዘሐራ ከኢራናውያን ጓደኞቿ ጋር እራት እየበሉ ስለ መዋዋቢያ ምርቶች ሲያወሩ ነበር የኩል ታሪክ እና ባህላዊ ሚና ትኩረቷን የሳበው።
"ኩል ለሴቶች ትልቅ ዋጋ አለው። በሌሎች አገራት የሚኖሩ ወይም የተገለሉ ሴቶች ቢሆኑም ለኩል ቦታ አላቸው" ትላለች።
ኩል ከመዋቢያነት ባሻገር
የኩል መነሻ ጥንታዊ የግብፅ፣ ሜሶፖታሚያ እና ፋርስ ሥልጣኔ ነው። ፆታ እና መደብ ሳይለይ ሁሉም ሰው የሚጠቀመው ነበር።
"ኩል ከመዋቢያነት በላይ ጥቅም ይሰጣል። መንፈሳዊ ዋጋ አለው። ዐይንን ከሕመም ለመከላከልም ይውላል" ትላለች ዘሐራ።
ጥንታዊ ግብፃውያን ሲቀበሩ ከኩል ጋር ነው። "ወደ ቀጣዩ ሕይወት" ይዘውት ሊጓዙ መፈለጋቸው ያለውን ትልቅ ዋጋ ያሳያል።
ከኩል ጋር በተያያዘ የመጀመሪያዋ 'ተጽዕኖ ፈጣሪ' ልንላት የምንችለው ንግሥት ነፈርቲቲን ነው።
በሉግዊግ ቦርቻት የተመሩ ጀርመናውያን የቅሪተ አካል አጥኚዎች ግብፅ ውስጥ ምርምር ካደረጉ በኋላ በአውሮፓውያኑ 1912 ይፋ ባደረጉት ግኝት መሠረት ንግሥት ነፈርቲቲ ኩል እንደምትቀባ ማስረጃ ተገኝቷል።
"የነፈርቲቲ ቅንድብ የተቀለበሰ ነው። በትክክል ቅርጹን ይዞ ሰማያዊ ቀለም ሽፋሽፍቷ ላይ ይታያል። የተቀባችው ኩል ነው የሚሆነው። ቀለሙ ቢለያይም ከአጠቃላይ ገጽታዋ ጋር ይናበባል" ስትል ዘሐራ በመጽሐፏ አስፍራለች።
ኩል በመቀባት የጀርመን ሴቶች የነፈርቲቲን ውበት ለመላበስ ሞክረዋል። ከውበት ባሻገር ኃያልነት እና መሪነትም ከኩል ጋር ይተሳሰራሉ።
ነፈርቲቲ ራሷን ያስዋበችበት መንገድ ዛሬም ድረስ ፋሽን ነው።
የንግሥቲቷን ገጽታ ማስመሰል የሚቻልበትን መንገድ ዩትዩብ፣ ቲክቶክ እና ኢንስታግራም ላይ የሚያስተምሩ ይዘት ፈጣሪዎች በመቶዎች ይቆጠራሉ።
ኩል በተለያዩ አገራት
ዘሐራ ለጥናቷ የተለያዩ አገራት ተጉዛለች። ካርላ፣ ቻድ፣ ሜክሲኮ እና ዮርዳኖስ ይገኙበታል። ኩል በተለያየ መንገድ ጥቅም ላይ እንደሚውል አስተውላለች።
ኩልን ከፀሐይ ወይም 'ከቡዳ' ለመከላከል የሚያውሉት አሉ። እንደ መንፈሳዊ ክንውን ወይም እንደ መድኃኒት የሚጠቀሙበት ማኅበረሰቦችንም አይታለች።
በጃፓን ባህላዊ ሙዚቀኛ እና ተወዛዋዥ የሆኑት ጌሻዎችን አነጋግራለች። ኩልን ራሳቸውን ለመጠበቅ የሚያውሉት ሲሆን፤ ቀይ ኩል ያዘወትራሉ።
በሜክሲኳዊ-አሜሪካውያኑ ቾላ ማኅበረሰብ ዘንድ ኩል የማንነት፣ የእምቢ ባይነት እና የኩራት መገለጫ ነው።
ኩል ግብፅን ጨምሮ በሌሎችም አገራት የሴቶች ብቻ ሳይሆን የወንዶችም መዋቢያ ነው። በቻድ የፉላኒ አርብቶ አደር ማኅበረሰብ የሆነው ዋዳቢ ውስጥ ዓመታዊ የወንዶች የቁንጅና ውድድር ይካሄዳል።
"በፔትራ የባዶይ ወንዶች እና በዮርዳኖስ ያሉ ወንዶችም ራሳቸውን ከፀሐይ ለመከላከል እና አምሮ ለመታየት ኩል ይጠቀማሉ" ትላለች ዘሐራ።
ወንዶች ፍቅረኛ እንደሌላቸው ለማሳየት እንዲሁም "ጉርምስናን ለማሳየት" ኩል እንደሚጠቀሙ ዘሐራ ትናገራለች።
በሌላ በኩል ልጆችን ኩል መቀባት ከለላ እንደሚሰጣቸው ይታመናል።
አረብኛ የሚናገሩ አገራት 'ኸጃል' እና 'ካኽሊላን' በሚሉ ቃላት ኩልን ይጠራሉ። ቃሉ የአክብሮት መገለጫም ነው።
ዩኔስኮ ለኩል ዕውቅና መስጠቱ ለአረቡ ዓለም አገራት እና አጠቃላይ የዓለም ደቡባዊ ክፍል ሕዝቦች ትልቅ ትርጉም እንዳለው ዘሐራ ትናገራለች።
እነዚህ ሕዝቦች ባህሉን ለዘመናት ጠብቀው ቆይተዋል። ቅኝ ግዛት ባህሉን እንዳያጠፋውም ተከላክለዋል።
"ኩል መቀባት መንፈሳዊ ክንውን ነው። ኩል ስንቀባ ባህላዊ ቅደም ተከተል አለን። ቅንድብ ወይም ሽፋሽፍት ላይ መስመር ከመቀባት ያለፈ ጥልቅ ትርጉም አለው" ትላለች ዘሐራ።
ከBBC አማርኛ የተወሰደ
እስኪ እናንተ አስተያየት ስጡበትና እኛ ሙያዊይ ማብራሪያ እንሰጥበታለን!