26/12/2025
" የቀን ወጫችን 3 ሚሊዮን ብር ሆኗል" - የክብር ዶክተር ቢንያም በለጠ
➡️ " በጤና ዙሪያ የጤና ባለሙያዎችን እገዛ እንፈልጋለን። መቄዶንያ ውስጥ ከ2500 በላይ የአዕምሮ ህሙማን ከ3000 በላይ የአልጋ ቁራኛ የሆኑ አሉ ! "
መቄዶንያ የአዕምሮ ህሙማንና አረጋዊያን መርጃ ማዕከል በየቀኑ 3 ሚሊዮን ብር ለማውጣት በመገደዱ፣ ያስጀመረው ሆስፒታል ባለመጠናቀቁ፣ በየክልል ከተሞች አዲስ ቅርንጫፎችን በመክፈቱ ለጋሽ እጆች የተለመደ ድጋፋቸውን እንዲያደርጉለት ጠይቋል።
ዛሬ ባካሄደው የውይይትና የምስጋና ፕግራም፣ ባለፈው አመት በርካቶች እንደተረባረቡበት አይነት በቀጥታ ስርጭት ድጋፍ የማሰባሰብ ስራ የፊታችን የካቲት 1 2018 ዓ/ም እንደሚካሄድ ገልጿል።
እስከዚያው ሁሉም መረጃውን በማዳረስ፣ መረጃውን የሚሰሙ ከወዲሁ ተዘጋጅተው የአቅማቸውን ድጋፍ እንዲያደርጉ ማዕከሉ ጥሪ አቅርቧል።
የካቲት 1/2018 ዓ/ም ገቢ የማሰባሰብ ሥራ ከባለፈው አመት የሚለየው በአሁኑ በመቄዶንያና በማንኛውም የግለሰቦች ዩቱብ በቀጥታ ስለሚተላለፍ መሆኑን የክብር ዶክተር ቢንያም በለጠ ገልጸዋል።
በዛሬ መርሃግብር የተገኘው ቲክቫህ ኢትዮጵያ፣ በበኩሉ፣ ባለፈው ዓመት የተሰባሰበ ገቢ ነበር፣ በግንባታ ላይ ያለው የሆስፒታል ህንፃ ከምን ደረሰ? አሁን የሚጎድላችሁ ነገር ምንድን ነው ? ሲል ጠይቋል።
የክብር ዶክተር ቢንያም በለጠ ለቲክቫህ ኢትዮጵያ ምን መለሱ ?
" ባለፈው ትልቅ የገቢ ማሰባሰቢያ አድርገን ወደ 900 ሚሊዮን ብር ሰብስበናል። 100 ቤቶች (ድጋፍ ተደርጓል)። እየተሰራ ያለው ህንፃው ግዙፍ ህንፃ ነው፤ ሆስፒታል ነው። ወጩ ብዙ ነው። አሁን ጤና ጥበቃ የሰጠን ፊገር አለ ወደ 6 ቢሊዮን ነው የሚፈጀመው ከእነኢኩፕመንት አሟልቶ ወደ ስራ ለማስገባት። አሁን ፎቁን ለመጨረስ በጣም ትንሽ ነው የቀረን።
ብር እንዲሰባሰብ የፈለግነው ሆስፒታሉን ለመጨመረስ፤ በየክልሎች ለጨመርናቸው 12 ቅርንጫፎች ብዙ ኮንስትራክሽን ስላሉ ለመስራት ነው። አስጨርሶ ሰው ለማስገባት ነው፤ ፎቁን ብቻ መጨረስ ሳይሆን ፈርኒቸርም አሟልተን ለሰዎች ዝግጁ ማድረግ ነው የቀረን።
አዲስ የተከፈቱት ቅርጫፎች ፦
- ቀብሪድሃር፣
- ሞያሌ፣
- ኮንሶ፣
- ዓዲግራት፣
- ዓድዋ፣
- አምቦ፣
- ጅማ፣
- ሞያሌ...በመሳሰሉት ቦታዎች የሚገኙ ነው። የተጀመሩ ህንፃዎችን እየሰራን ነው ቀብሪድሃር፣ አርባምንጭ፣ ላሊበላ እነርሱን መጨረስ አለብን።
ወጫችን ብዙ ነው፤ 56 ቦታ ሰዎችን ማኖር ማለት ነው። ቋሚ ገቢ የውጭ ፈንድ የሌለው፣ በቀን 3 ሚሊዮን ብር ወጭ ያለበት ማዕከል ነውና በጣም ከባድ ነው " ብለዋል።
ከህክምና አኳያ ችግር ካለ ስንጠይቃቸውም፣ የአዕምሮ ህሙማኑና አረጋዊያኑ ህክምና እንደሚያስፈልጋቸው ገልጸው፣ " የጤና ባለሙያ፣ የፊዚትራፒ፣ ነርሶች፣ ዶክተሮች እንፈልጋለን። በግል ሆስፒታሎች ያሉት በሳምንት አንዴ ቢረዱን በጣም ትልቅ እገዛ ነው። ትልቁ ነገር ህክምና ነው። የአልጋ ቁራኛ የሆነ ሰው የሚያስፈልገው ህክምና ነው " ብለዋል።
" በጤና ዙሪያ የጤና ባለሙያዎችን እገዛ እንፈልጋለን። መቄዶንያ ውስጥ ከ2500 በላይ የአዕምሮ ህሙማን ከ3000 በላይ የአልጋ ቁራኛ የሆኑ አሉ። ሌላው አረጋዊ፣ አካል ጉዳተኛ ነው" ሲሉም ለቲክቫህ ኢትዮጵያ ተናግረዋል።
የመቄዶንያ ወጭ በቀን 2 ሚሊዮን መሆኑን ማዕከሉ ከዚህ ቀደም መግለጹ ይታወሳል፤ አሁን ወጩ በምን ምክንያት እንደጨመረ ቲክቫህ የጠየቃቸው ቢንያም (የክብር ዶ/ር)፣ በአመት ውስጥ ብቻ አዳዲስ ቅርንጫፎች በመከፈታቸው መሆኑን በመጥቀስ አስረድተዋል።
የማዕከሉ የቀን ወጭ 3 ወደ ሚሊዮን ብር ከፍ ማለቱን፣ በተለይ በአዳዲሶቹ ብራንቾች ብዙ ስራዎች እንዳሉባቸው ገልጸው፣ ሰዎች በማዕከሉ ስልክ ቁጥር 09432020 እየደወሉ እንዲጎበኟቸው፣ ድጋፍ እንዲያደርጉ ጥሪ አቅርበዋል።
ቲክቫህ ኢትዮጵያ