11/05/2017
ህጻናት እንደ ስማርት ስልክ ያሉ መገልገያዎችን እንዲጠቀሙ ማድረግ የአፍ መፍቻ ጊዜያቸውን ያዘገያል- ጥናት
ህጻናት ልጆችን ለማባበልም ይሁን እንዲጫወቱ ለማድረግ ስማርት ስልካችንን እና ሌሎች የኤሌክትሮኒክስ መገልገያዎችን መስጠት የተለመደ ነው።
ይህ ተግባር ግን ትክክል አይደለም፤ ምክንያቱ ደግሞ ህጻናት ልጆች የቴክኖሎጂ ቁሳቁሶች ላይ ጊዜያቸውን እንዲያሳልፉ ማድረግ የአፍ መፍቻ ጊዜያቸውን ስለሚያዘገይ ነው ይለናል ከሰሞኑ የወጣ ጥናት።
ጥናቱ ከ6 ወር እስከ 2 ዓመት መካከል ያሉ ህጻናት እንደ ስማርት ስልክ፣ ታብሌት እና ኤሌክትሮኒክስ ጌሞች ላይ በሚያሳልፉት ጊዜ መጠን የአፍ መፍቻ ጊዜያቸውን እየዘገየ ይሄዳል የሚለውን አመልክቷል።
በካናዳ ቶሮንቶ የህጻናት ሆስፒታል የተካሄደው ጥናት ላይ 900 ህጻናት እንዲሳተፉ የተደረገ ሲሆን፥ ልጆቹ እድሜያቸው 1 ዓመት ከ6 ወር እስኪሞላ ድረስ ምን ያክል ጊዜን ከሞባይል እና ሌሎች የኤሌክትሮኒክስ መገልገያዎች ጋር እንደሚያሳልፉ ወላጆቻቸው ተጠይቀዋል።
በመቀጠልም ተመራማሪዎቹ ህጻናቱ በ1 ከ6 ወር እድሜያቸው የመናገር ችሎታቸው እና ቋንቋን የመጠቀም ክህሎታቸው ምን ያክል ጨምሯል የሚለውን ለመለየት የሚረዳ መሳሪያ ተጠቅመው ለክተዋል።
በዚህም ህጻናቱ ከሌሎች ትኩረት ለማግኘት ሲሉ ቃላቶችን እንዴት አንድ ላይ ጠምረው ይጠቀማሉ፤ እንዲሁም ምን ያክል ቃላትን ይጠቀማሉ የሚለውን አይተዋል።
በጥናቱ ላይ ከተሳተፉ ህጻናት ውስጥ 20 በመቶ ያክሉ በቀን ውስጥ በአማካኝ 28 ደቂቃ ያክል በስማርት ስልኮች እና ሌሎች መገልገያዎች ላይ ጊዜያቸውን እንደሚያሳልፉ ጥናቱ ለይቷል።
ህጻናቱ በስክሪን ላይ የሚያሳልፉት ጊዜ በ30 ደቂቃ እየጨመረ በሄደ ቁጥር አፍ የመፍቻ ጊዜያቸው የመዘግየት እድል ደግሞሞ በ49 በመቶ እየጨመረ እንደሚሄድም ተመራማሪዎቹ በጥናታቸው ውጤት ላይ አስፍረዋል።
በካናዳ ቶሮንቶ የህጻናት ሆስፒታል የአጥኚዎች ቡድን መሪ ዶክተር ካትሪን በይርከን፥ “ተንቀሳቃሽ የሆኑ የኤሌክትሮኒክስ መገልገያዎች የህጻናት የመግባባት ጊዜ ላይ መዘግየትን እንደሚያስከትል የለየው ጥናት እስካሁን ከተሰሩት በአይነቱ የመጀመሪያ ነው” ብለዋል።
“ሆኖም ግን የጥናቱን ውጤት አሁንም በጥልቀት ማየት ይኖርብናል፤ ምክንያቱ ደግሞ አሁን ያገኘነው ውጤት ገና የመጀመሪያ ምልከታ ስለሆነ ነው” ሲሉም ተናግረዋል።
እንደ አውሮፓውያኑ አቆጣጠር በ2013 የወጣ ሪፖርት እንደሚያመለክተው እንደ ሞባይል ስልክ ያሉ ተንቀሳቃኝ የኤሌክትሮኒክስ መገልገያዎችን የሚጠቀሙ ህጻናት ቁጥር በ2011 ከነበረበት 10 በመቶ ወደ 40 በመቶ ከፍ ብሏል።
አሁን ላይ ደግሞ የስማርት ስልኮች በዓለም ዙሪያ በብዛት ጥቅም ላይ መዋል መጀመራቸውን ተከትሎ ይህ አሀዝ በእጥፍ ሊጨምር እንደሚችል ተገምቷል።
ታዲያ ወላጆችም ልጆቻቸው እንደ ስማርት ስልክ፣ ታብሌት እና ሌሎች የኤሌክትሮኒክስ መገልገያዎች ላይ የሚያሳልፉትን ጊዜ መገደብ መልካም ነው፤ ልጆች ከኤሌክትሮኒክስ መገልገያዎች ውጭ ተፈጥሯዊ በሆነ መልኩ እንዲጫወቱም ማድረግም ይመከራል።
ምንጭ፦ http://edition.cnn.com/
View the latest news and breaking news today for U.S., world, weather, entertainment, politics and health at CNN.com.