06/12/2025
በሲዳማ ክልል ህፃናት እንደተወለዱ በ24 ሰአት ውስጥ የሚሰጠው የጉበት በሽታ ሄፓታይተስ ቢ ቫይረስ መከላከያ ክትባት በይፋ ተጀምሯል ።
ህጻናት እንደተወለዱ የሚሰጠው የጉበት በሽታ መከላከያ ክትባት አገልግሎት በማስጀመሪያ መርሐ ግብር በሲዳማ ክልል በሀዋሳ ከተማ አላሙራ የመጀመሪያ ደረጃ ሆስፒታል በይፋ ተጀምሯል።
በማስጀመሪያው መርሐ ግብር ላይ የተገኙት የሲዳማ ክልል ጤና ቢሮ ምክትልና የጤና ፕሮግራም ዘርፍ ሀላፊ አቶ በላይነህ በቀለ እንደተናገሩት ፦ጥራቱን የጠበቀ የክትባት ተደራሽነትን ማረጋገጥ ጤናማ ማህበረሰብ ለመፍጠር ለሚደረገው ጥረት ሚናው የላቀ መሆኑን ገልፀዋል ።
እንደ ሀገርም ሆነ እንደ ክልል የጉበት ቫይረስ በሽታን ስርጭትን ለመቀነስ ብሎም ለማጥፋት እቅድ ተይዞ እየተሰራ እንደሚገኝ የገለፁት አቶ በላይነህ ፤ ለዚህም ህፃናት እንደተወለዱ በ24 ሰአት ውስጥ ለሚሰጠው የጉበት በሽታ ሄፓታይተስ ቢ ቫይረስ መከላከያ ክትባት ሁሉም ትኩረት ሊሰጠው እንደሚገባ አሳስበዋል።
የጉበት በሽታ ከሚተላለፍባቸው ዋነኛ መንገዶች መካከል ከእናት ወደ ልጅ መሆኑን የተናገሩት አቶ በላይነህ ሕፃናትን እንደ ተወለዱ ክትባቱን እንዲወስዱ ማድረግ ዋነኛ የመከላከያ መንገድ መሆኑን ተናግረዋል ።
የጉበት በሽታ መከላከያ ክትባቱ ከዛሬ ጀምሮ በመደበኛ ክትባት መርሐ ግብር ተካትቶ መሰጠት እንደሚጀምርም ገልጸዋል።
በሁሉም ጤና ተቋማት ጥራቱን ጠበቀ መልኩ በመደበኛ የክትባት ፕሮግራም አስገብተው ክትባቱን እንዲሰጡ ያሳሰቡ ሲሆን ፤ ወላጆች ልጆቻቸውን እንደ ወለዱ ህጻናት በ24 ሠአት ውስጥ እንዲያስከተቡ ለወላጆች ጥሪአቸውን አስተላልፈዋል ።
በፕሮራሙ ላይ ከሲዳማ ክልሉ ጤና ቢሮ ፣ከአላሙራ የመጀመሪያ ደረጃ ሆስፒታል፣ ከጤና መምሪያ እንዲሁም ከጤና ጽ/ቤት ኃላፊዎችና የዘርፉ ባለሙያዎች ተገኝተዋል::